መስከረም 9 2018 - መድሀኒቶችና የህክምና ቁሳቁሶች ከግምጃ ቤት ጀምሮ እስከ ስርጭት ድረስ ከፍተኛ ቁጥጥር እንዲደረግበት የሚያስችል የዲጅታል ሥርዓት ሊዘረጋ መሆኑ ተሰማ
- sheger1021fm
- Sep 19
- 1 min read
በኢትዮጵያ በሁሉም ክፍሎች መድኃኒቶችንና የህክምና ቁሳቁሶችን የመግዛት፤ የማከማቸት እና የማከፋፈል ኃላፊነት የተሰጠው የኢትዮጵያ የመድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ይህ መንገድ የስራዬን ትክክለኝነት ያረጋግጥልኛል ብሏል።
በኢትዮጵያ የመድኃኒት ቁጥጥር እንዲሻሻል እና ከፍተኛ ሐብት የወጣበት ሐብት ቆጠራ ሥርዓት ትክክለኛነት እንዲረጋገጥ ይህ የዲጂታል መንገድ እንደሚያግዝ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ ስማርት የዲጂታል ጤና አቅርቦትና ሰንሰለት ለመዘርጋት ኢትዮ ቴሌኮምና የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ውል ማሰራቸውን ሰምተናል።

ይህ ሥርዓት የኢትዮጵያን ብሔራዊ የመድኃኒት አቅርቦትና የህክምና እቃዎችን ፍሰት የሚያቀላጥፍ መንገድ ነው ተብሏል።
በመረጃ የተደገፈ የአቅርቦት ሰንሰለቱን በአጭር ጊዜ ለመዘርጋትም መንገድ መጀመሩን የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ የኢንተርፕራይዝ ሶሉሽን ኦፊሰር አቶ ዮሐንስ ጌታሁን ተናግረዋል።
መፍትሄው ሐገር በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የምታስገባው መድሀኒትና የንብረት ቆጠራ ሥርዓትን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ ያግዛል መባሉን ሰምተናል።
ይህ ወጥ ስማርት የአቅርቦት ሰንሰለት መፍትሄ አንድ ወጥ አሰራርና ቁጥጥር እንዲኖር በአንድ ማዕከል ፕላትፎርም አማካኝነት አፋጣኝ የኦፕሬሽናል መረጃ ዳታ እና የቅድመ አደጋ ማንቂያዎችን በመጠቀም ፈጣን ውሳኔ እና ለሚከሰት አደጋ ቀልጣፋ ምላሽ ለመስጠት እንደሚያግዝ ዶ/ር መቅደስ አስረድተዋል።
በተለይ አገልግሎቱ መድኃኒት በሚከማችባቸው አካባቢዎች ፤ መጋዘኖች ፤ ተሽከርካሪዎችና አጠቃላይ ሁኔታ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የሚደገፍ የደህንነት ጥበቃ እንደሚደረግለት ሰምተናል።
ይህ መንገድ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችና የባዮ ሜትሪክ ናሙናዎችን በመጠቀም በግምጃ ቤትና ቢሮዎች ማን እንደገባና እንደወጣ በዘመናዊ ስማርት የጎብኚዎች የማንነት መለያ እና የምዝገባ ሥርዓት ለመቆጣጠር የሚቻልበት እንደሆነ መፍትሄ አቅራቢዎቹ አስረድተዋል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ….
ተህቦ ንጉሴ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments