top of page

መስከረም 21 2018 - በስራ ላይ በተሰማሩ ደንብ አስከባሪዎች ላይ በተለያየ ጊዜ በሚደርስ ድብደባ ህይወታቸው ያለፈ ሰራተኞች እንዳሉ የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ተናገረ

  • sheger1021fm
  • Oct 1
  • 1 min read
ree

ባለስልጣኑ በአዲስ አበባ ከተማና በአካባቢዋ የደንብ ጥሰቶችን ለመቆጣጠር ተሰማርተው በሚሰሩ ደንብ አስከባሪዎች ላይ ተደጋጋሚ ድብደባ እየተፈጸመባቸው እንደሆነ ተናግሯል።

በዚህም ህይወታቸው ካለፈ ሰራተኞች በተጨማሪ በድብደባ ጉዳት የደረሰባቸው ሰራተኞች ሆስፒታሎች ውስጥ እንደሚገኙም ባለስልጣኑ ሲናገር ሰምተናል።

የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ንጋቱ ዳኛቸው በባለስልጣኑ ስር ያሉት አብዛኞቹ ደንብ አስከባሪዎች ስራቸውን የሚከውኑት ህጉን በተከተለ መልኩ ቢሆንም ደንብ ተላላፊዎች ህግን በሚያስከብሩ ሰራተኞቻችን ላይ ድብደባ እየፈፀሙባቸው ነው ብለዋል ።

በዚህም ሰራተኞቻችን ከአካል ጉዳት እስከ ሞት ድረስ መስዋዕትነት እየከፈሉ ነው ይላሉ።

አንዳንድ ደንብ አስከባሪዎች ህግን ባልተከተለ መልኩ በመንገድ ዳር በንግድ የተሰማሩ አካላት ላይ የማዋከብ፣አካላዊ ድብዳባ የመፈጸመ፣ እቃዎቻቸውን የመሰባበር ድርጊቶችን ሲፈጸሙ ይታያል።

ደንብ ተላልፈዋል ባሏቸው ግለሰቦች ላይ የሚፈጽሟቸውን ህገወጥ ድርጊቶች በተንቀሳቃሽ ምስል የተቀረጹ ምስሎችም በማህበራዊ ሚዲያዎች ሲዘዋወሩ እንመለከታለን ።

ለመሆኑ ይህን ጉዳይ እንዴት ታዩታላችሁ? እነኝህን አካላትስ ተጠያቂ ከማድረግ አኳያ ምን እየሰራችሁ ነው ? ብለን ጠይቀናል።

አብዛኞቹ ደንብ አስከባሪዎች የደንብ ጥስቶችን የሚቆጣጠሩት ህጉን በተከተለ መልኩ ነው ሲሉ አቶ ንጋቱ ነግረውናል ። ይሁን እንጂ ቁጥራቸው አነስተኛ ቢሆንም አንዳንድ ደንብ አስከባሪዎች ከህግ ባፈነገጠ መልኩ ሊሰሩ ይችላሉ ብለዋል።

ማህበረሰቡም ጥቆማ ከሰጠን ህጉን በተላለፉ ደንብ አስከባሪዎች ላይ አስፈላጊውን እርምጃ እንወስዳለን የሚል ምላሽ ሰጥተውናል።

በከተማዋ በተለይ በትምህርት ቤቶች አቅራቢያ የሚካሄዱ አዋኪ ድርጊቶች ማለትም እንደ ሺሻ ቤቶች፣ ቁማር ቤቶች ፣ ጭፈራና መጠጥ ቤቶች ላይ እየተደረገ ባለው ጥብቅ ቁጥጥር ምክንያት ችግሩ መቀነስ አሳይቷል፣መሻሻልም አምጥቷል ሲሉ አቶ ንጋቱ ነግረውናል ።

ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ… https://youtu.be/6VmQGCQm194


Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2025 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page