መስከረም 16 2018 - የውጪ ሀገራት ወሬዎች
- sheger1021fm
- Sep 26
- 2 min read

የእስራኤል የጦር በየመኗ ርዕሰ ከተማ ሰንዓ ከባድ የአየር ድብደባ ፈፀመ ተባለ፡፡
በድብደባው ከ10 የማያንሱ የእስራኤል የጦር አውሮፕላኖች መካፈላቸው ታውቋል፡፡
ከየመን ሁቲዎች ጋር ቅርበት አለው የሚባለው አል ማስሪ የተሰኘው ቴሌቪዥን በሰንዓ ድብደባ መፈፀሙን እንደዘገበ አልጀዚራ ፅፏል፡፡
የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ በሰንዓ የሁቲዎቹ ዋነኛ የጦር ማዘዣ ላይ ድብደባ ፈፅመናል ማለቱ ተሰምቷል፡፡
የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ በበኩላቸው በአስራዎች የሚቆጠሩ ቀንደኛ የሁቲ አሸባሪዎችን ገድለናል ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ፅፈዋል፡፡
በሰንዓ ድብደባው የተፈፀመው የሁቲዎቹ መሪ አብዱል መሊክ አል ሁቲ በቴሌቪዥን ንግግር እያደረጉ በነበረበት ወቅት ነው ተብሏል፡፡
እስራኤል በሰንዓ ድብደባ የፈፀመችው ሁቲዎች በእስራኤሏ ኤይላት ከተማ የድሮን ጥቃት ከፈፀሙ ከ1 ቀን በኋላ እንደሆነ መረጃው አስታውሷል፡፡

የፈረንሳዩ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ሳርኮዚ ከውጭ በህገ-ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ለምርጫ ዘመቻ በማዋል ወንጀል ጥፋተኛ ተብለው የ5 አመታት የእስር ቅጣት ተፈረደፈባቸው፡፡
ሳርኮዚ በህገ-ወጥ መንገድ ከቀድሞው የሊቢያ መሪ ኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊ በሚሊዮኖች ዩሮ የሚቆጠር ገንዘብ መቀበላቸው ተራግጦባቸዋል ተብሏል፡፡
የፈረንሳይ ህግ ከውጭ የተገኝን ገንዘብ ለምርጫ ዘመቻ ማከናወኛነት ማዋልን እንደሚከለክል በመረጃው ተጠቅሷል፡፡
ሳርኮዚ ከ8 አመታት በፊት ገንዘቡን ከጋዳፊ በህገወጥ መንገድ የተቀበሉት የቀድሞውን የሊቢያ መሪ ከአውሮፓ መሪዎች ለማስታረቅ እና የአስተዳደራቸውን ገፅታ ለማሻሻል ተስማምተው ነው ተብሏል፡፡
የፈረንሳይ የቀድሞ ፕሬዘዳንት የተላለፈባቸውን የ5 አመታት የእስር ቅጣት ለማስቀልበስ ይግባኝ እንደሚጠይቁ ተናግረዋል፡፡
ይግባኛቸው ቁርጡ እስኪለይለትም በእስር ሆነው ጉዳያቸውን እንደሚከታተሉ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
የፈረንሳይ ባህር ሀይል በምዕራብ አፍሪካ የባህር ዳርቻ 10 ቶን ያህል አደገኛ ዕፅ መያዙን የአውሮፓዊቱ አገር ሹሞች ተናገሩ፡፡
በሁለቱ የፈረንሳይ ባህር ሀይል መርከቦች አስገዳጅነት 10 ቶን ያህሉ ኮኮይን የተሰኘ አደገኛ እፅ የተያዘው መለያ ከሌለው ዓሣ አስጋሪ ጀልባ እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
በአካባቢው ባለፉት 9 ወራት 54 ቶን አደገኛ እፅ መያዙን መረጃው አስታውሷል፡፡
የምዕራብ አፍሪካው የጊኒ ባህረ ሰላጤ ወንጀል በዛሽ መሆኑ ይነገራል፡፡
በአሁኑ ወቅት የአካባቢው የአደገኛ እፅ ማስተላለፊያ መሆን እየጨመረ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
ከዓመት በፊትም የፈረንሳይ ባህር ሀይል በዚሁ ስፍራ 11 ቶን ያህል አደገኛ እፅ መያዙ ለትውስታ ተነስቷል፡፡

በጊኒ ቢሳዎ ዋነኛው የመንግስት ተቃዋሚዎች ጥምረት በፓርላማ ምርጫው እንዳይካፈል በፍርድ ቤት ተከለከለ፡፡
በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በፓርላማ ምርጫው እንዳይካፈል የተከለከለው የተቃዋሚዎች ጥምረት 10 የፖለቲካ ማህበራትን ያሰባሰበ እንደሆነ አፍሪካ ኒውስ ፅፏል፡፡
ጥምረቱ ስለ ክልከላው ከጠቅላው ፍርድ ቤቱ ማብራሪያ እሻለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡
የዋነኛው የተቃዋሚዎች ጥምረት በፓርላማ ምርጫው እንዳይካፈል መከልሉ በአገሪቱ ፖለቲካዊ ቀውስ መቀስቀሱ እንደማይቀር ተገምቷል፡፡
ፕሬዘዳንት ኡማሮ ሲስኮ ኢምባሎ በአሁኑ ወቅት አምባገነናዊ የአመራር መላ ስራ ላይ ማዋላቸው ይነገራል፡፡
ባለፈው ዓመት የካቲት ወር የመንግስት ግልበጣ ተሞክሮባቸው እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
የኔነህ ከበደ የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments