ሕብረት ኢንሹራንስ በ2017 በጀት ዓመት በታሪኬ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢሊዮን የሚቆጠር ትርፍ አገኘሁ አለ።
- sheger1021fm
- 4 minutes ago
- 2 min read
ህዳር 26 2018
ሕብረት ኢንሹራንስ በ2017 በጀት ዓመት በታሪኬ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢሊዮን የሚቆጠር ትርፍ አገኘሁ አለ።
በአንድ አክሲዮን የተመዘገበው ትርፍ 68.55 በመቶ መሆኑን ኩባንያው ዛሬ ባካሄደው ዓመታዊ የባለ አክሲዮኖች ጉባኤ ላይ ያቀረበው ሪፖርት ተናግሯል።
ሕብረት ኢንሹራንስ በ2017 በጀት ዓመት ከግብር በፊት 1 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን የተናገረ ሲሆን ይህም ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ79 በመቶ ጭማሬ አሳይቷል ብሏል።
ኩባንያው ከግብር በኋላ ያገኘው የተጣራ ትርፍ 843 ሚሊዮን ብር ሲሆን ይህም ከቀዳሚው አመት ጋር ሲነፃፀር በተመሳሳይ የ79 በመቶ እድገት ማሳየቱን ከሪፖርቱ ተመልክተናል።
በአንድ አክሲዮን የተመዘገበው ትርፍ (Earnings Per Share) አምና ከነበረው በ47.78 ከመቶ ወደ 68.55 ከመቶ ከፍ ያለ ሲሆን በንጽጽር ሲታይ የ43.5 ከመቶ እድገት አሳይቷል፡፡
ሕብረት ኢንሹራንስ ከሁሉም የኢንሹራንስ ዘርፎች የሰበሰበው አጠቃላይ አረቦን 2.75 ቢሊዮን ብር ሲሆን አምና ከተገኘው የ40.31 ከመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡

ከተሰበሰበው አጠቃላይ የአረቦን መጠን ውስጥ አብዛኛው ወይንም 2.57 ቢሊዮን ብር ሕይወት ነክ ካልሆነው የኢንሹራንስ ዘርፍ፣ 141 ሚሊዮን ብር ከሕይወት ኢንሹራንስ ቀሪው ብር 31.9 ሚሊዮን ብሩ ደግሞ ከታካፉል ኢንሹራንስ የተገኘ መሆኑ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ኩባንያው አገኘሁት ያለው የተጣራ የኢንቨስትመንት ገቢ 544 ሚሊዮን ብር ነው።
ኩባንያው በበጀት ዓመቱ ያስመዘገበው የኢንሹራንስ አገልግሎት ውጤት በ2016 ከነበረው በ77.63 ከመቶ ዕድገት በማስመዝገብ 765 ሚሊዮን ደርሷል ተብሏል።
የኩባንያው የተከፈለ ካፒታል 1.34 ቢሊዮን ብር፣ ጠቅላላ ሃብቱ ደግሞ ከ6 ቢሊየን ብር በላይ መድረሱ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ሕብረት ኢንሹራንስ የ2017 በጀትን ዓመት በስኬት ያጠናቀኩት የተለያዩ ችግሮችን ተቋቁሜ ነው ብሏል።
የፀጥታ ችግር፣ የዋጋ ግሽበት፣ የብር የመግዛት አቅም ማሽቆልቆል፣ የኢንቨስትመንት መቀዛቀዝ፣ የጥሬ ገንዘብ እጥረት እና የባንክ ብድር መገደብ ወይም እንደሚፈለገው አለመሆንን ዋና ዋና ችግሮች ብሎ ጠቅሷል።
በኢንሹራንስ ኩባንያዎች መካከል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣው ፉክክር እና የተሽከርካሪዎች ኢንሹራንስ በተመለከተ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ቁርጥ የዐረቦን ተመን እንዲሁም በኢንደስትሪው አልፎ አልፎ የሚታየው ስነ ምግባር የጎደለው የንግድ ስራ እንቅስቃሴ
በዓመቱ ያጋጠሙ ተጨማሪ ፈተናዎች ነበሩ ሲልም አስረድቷል፡፡
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
👇👇👇
🌐Website፡ https://www.shegerfm.com/
🎥YouTube https://tinyurl.com/37tux478
🟦Telegram https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📘Facebook፡ https://tinyurl.com/4tx8t8wm
💬WhatsApp https://tinyurl.com/ycxjmm3s








