ሐምሌ 8 2017 - በአዲስ አበባ እና በሌሎችም አካባቢዎች በቀጣዮቹ 10 ቀናት የሚኖረው ከበድ ያለ የዝናብ ጎርፍ ሊያስከትል ይችላል ተባለ
- sheger1021fm
- Jul 15
- 1 min read

ይህንን ያለው የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት እየጣለ ያለው ዝናብ ከበድ ብሎ እንደሚቀጥል የቅድመ ትንቢያ መረጃዎች እንዳሳዩና ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስቧል፡፡
በኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር )እንደነገሩን የክረምቱን መግባት ተከትሎ ባለፉት 10 ቀናት አዲስ አበባን ጨምሮ 70 በሚደርሱ ከተሞች ከ30 እስከ 114 ሚሊ ሜትር የደረሰ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ተመዝግቧል፡፡
በመጪዎቹ ቀናትም የዝናቡ መጠን ጠንከር እንደሚል የትንበያ መረጃዎች ያመለክታሉ ያሉን ዋና ዳይሬክተሩ በአካባቢዎቹ ጎርፍ ሊኖር ስለሚችል በተለይ በአዲስ አበባ የውሃ ማፋሰሻ ቱቦዎች መዘጋት እንዳይኖር ለከተማ አስተዳደሩ የአደጋ ተከላካይ መስሪያ ቤት ለጥንቃቄ እንዲሆን የትንቢያ መረጃዎችን እየሰጠን ነው ብለዋል፡፡
በአብዛኛው እየጣለ ያለው የክረምቱ ዝናብ ጥሩ የሚባል ነው መሆኑን የሚያነሱት ሃላፊው የዝናቡ መጠን በተለይ ውሃ መያዝ ላለባቸው የሃይል ማመንጫ ግድቦች የተመቸ፤ለሰብሎች እድገት ጠቃሚ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡
እስካሁን ባለው የትንቢያ መረጃ የአቪዬሽኑን ዘርፍ ሊያውክ የሚችል የአየር ሁኔታ የለም ሲኖር ቀድመን እናሳውቃለን ብለዋል፡፡
ከበድ ያለ ዝናብ የሚያስተናግዱ አካባቢዎች ያሉ እያደጉ ያሉና የደረሱ ሰብሎች ጉዳት እንዳደርስባቸው የውሃ ማፋሰሻ ቦዮችን ከማዘጋጀት ጀምሮ በማሳዎች ላይ ጥንቃቄ ይደረግ ሲል ኢንስቲትዩቱ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡
ምንታምር ፀጋው












Comments