ሐምሌ 25 2017 - ''የመሬት መንሸራተት እንዳይከሰት ስራዎችን እየከወንኩ ነው'' ጎፋ ዞን
- sheger1021fm
- Aug 1
- 1 min read
በጎፋ ዞን ዳግም የመሬት መንሸራተት አደጋ እንዳይከሰት ስራዎችን እየከወነ ቢሆንም የአቅም ውስንነት ግጥሞኛል ሲል የጎፋ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ተናገረ።
በዞኑ የመሬት መንሸራተት አደጋ ዳግም እንዳይከሰት ለቅድመ አደጋ መከላከል ስራ መከወኛ ከተለያዩ አካላት ድጋፍን እንሻለን ብሏል።
ባለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ላይ በጎፋ ዞን ተከስቶ የነበረው የመሬት መንሸራተት አደጋ ከ220 በላይ የሚሆኑ ሰዎችን ህይወት ነጥቋል።
በርካታ መኖሪያ ቤቶችንም አወድሟል።
የዞኑ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ጥሪም ይህ አደጋ ዳግም እንዳይከሰት በማሰብ እንደሆነም ኮሚሽኑ ነግሮናል፡፡
ኮሚሽኑ በዚህ ክረምትም በአንዳንድ ቦታዎች ላይ አልፎ አልፎ የመሬት ናዳ እየተከሰተ እንደሆነም የተናገረ ሲሆን በሰዎች ላይ ግን ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳላስከተለ ሰምተናል፡፡
በዞኑ የተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ ዳግም እንዳይከሰት በኮሚሽኑ በኩል የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎችን እና የቅድመ አደጋ መከላከል ስራዎች እየተከወነ ነው ያሉት የጎፋ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ማርቆስ መለሰ ነግረውናል።

ነገር ግን አሁን እየተሰራ ያለው ስራ በበጀት እጥረት ምክንያት በቂ አይደለም ይላሉ።
ባለፈው ዓመት ተከስቶ በነበረው የመሬት መንሸራተት አደጋ የአደጋው ሰለባ የሆኑ ሰዎችን ከእለት ድጋፍ ባለፈ በዘላቂነት የማቋቋም ስራዎች እየተከወኑ መሆኑንም አቶ ማርቆስ ነግረውናል።
በዞኑ በጎፋ ዞን በመሬት መንሸራተት አደጋ ቤት ንብረታቸው ከወደመባቸው መካከል 80 በመቶ የሚሆኑት ቤታቸው እንደተገነባላቸው እና በዘላቂነት የሚቋቋሙበት ሁኔታ እንደተፈጠረላቸውም ሰምተናል።
ፍቅሩ አምባቸው











Comments