ሐምሌ 12 2017 - በሕግ ጥላ ሥር ያሉ ዜጎች በምክክር ሂደቱ እንዲሳተፉ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የምክክር ኮሚሽን ተናገረ።
- sheger1021fm
- Jul 19
- 1 min read
ኮሚሽኑ በወቅታዊ የሥራ እንቅስቃሴዎቹ ዙሪያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ቃል አቀባይ አቶ ጥበቡ ታደሠ በመግለጫቸው በሕግ ጥላ ሥር ያሉ ዜጎች በምክክር ሂደቱ የሚሳተፉበትና ሀሳባቸው የሚደመጥበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ኮሚሽኑ ጥረቱን አጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል።

ኮሚሽኑ በሕግ ጥላ ሥር ያሉ ዜጎች በምክክር ሂደቱ ቢሳተፉ የሂደቱን አሳታፊነትና አካታችነት ይበልጥ ያጠናክራል የሚል እምነት እንዳለው የተናገሩት ቃል አቀባዩ፤ በማረሚያ ቤት ያሉ ወገኖች የሚሰጡት የአጀንዳ ግብዓት ካሉበት አውድ አኳያ የራሱ መልክ ስላለው ለምክክር ሂደቱ በእጅጉ እንደሚጠቅም አስረድተዋል።
የኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች ከፌደራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽነር ጋር ታራሚዎች በምክክር ሂደቱ መሳተፍ በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውም በመግለጫው ተነስቷል፡፡
ከክልል ማረማያ ቤት ኃላፊዎች ጋር ለመወያየት ዕቅድ ስለመያዙም ቃል አቀባዩ ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል ኮሚሽኑ በምክክር ሂደቱ ሲሳተፉ ቆይተው አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎችን በማስቀመጥ ከተሳትፎ ከታቀቡ ሦስት የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ውይይት ማድረጉንም ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው አንስተዋል።
ፓርቲዎቹም ኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)፣ መላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና እናት ፓርቲ መሆናቸው ተነግሯል።
ፓርቲዎቹ ያነሷቸው ጉዳዮች መፍትሔ ማግኘት እንዳለባቸው ኮሚሽኑ እንደሚያምንም ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።
በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ኮሚሽኑ በአዋጅ ከተሰጡት ተግባርና ኃላፊነቶች ውጭ መሆናቸውን ከኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያሳያል።
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments