top of page

ግንቦት 2፣2016 - ስታርት አፕ(Start UP)ን በኢትዮጵያ ተግባር ላይ ለማዋል ብዙ መስራት ይጠይቃል ተባለ

ስራ ፈጣሪዎችን ለማበረታታት ያግዛለ በሚል መመሪያ የወጣለት ስታርት አፕ(Start UP) ተግባር ላይ ለማዋል ብዙ መስራት ይጠይቃል ተባለ፡፡


በተለያዩ መስኮች የሚመነጩ የፈጠራ ሀሳቦችን ወደ ተግባር ለማውረድ መንገድ ያቃናል በሚል እየተወራ ያለ ጉዳይ ነው ሰታርት አፕ፡፡


በተለይ በአሁን ወቀት ለሀገር አስፈላጊ እንደሆነ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጀምሮ በተለያዩ የዘርፉ አካላት ተደጋግሞ እየተነገረለትም ነው፡፡


የስታርት አፕ ሀሳብ ሲፍታታ፤ ለስራ ፈጣሪዎች የተመች ከባቢን መፍጠር፣ ችግር ፈቺ መስኮች ላይ አተኩሮ መስራት፣ ለዘርፉ የተስማሙ ፖሊሲዎችን አፅድቆ ድጋፍ ማድረግና ተያያዥ ጉዳዮችን ያጠቃልላል፡፡

ይህ ሀሳብ ለዓመታት በተለያዩ አካላት እየተነሳ ቢቆይም ትኩረት ተሰጥቶት ባለመሰራቱ በወጣቶች የመነጩ የስራ ሀሳቦች መሬት ላይ ወርደው ጠቃሚ መሆን ሳይችሉ ቀርተዋል ተብሏል፡፡


ዘርፉ የሚመራበት ህግም በሀገሪቷ አለመኖር ዋነኛው ችግር ሆኖ መቆየቱ ተነግሯል፡፡


መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሀሳቡ ጠቃሚነት ተረደቻለሁ ብሎ፤ በሚመለከታቸው አካላት የቀረቡለትን፤ ዘርፉን እና ተያያዥ መስኮችን የሚደግፉ 11 መመሪያዎችን አስተዋውቋል፡፡


ይሁን እንጂ እነዚህ ይፋ የተደረጉ መመሪያዎች ወደ ተግባር ለማውረድ ገና ብዙ መስራት እንደሚጠይቅ ተነግሯል፡፡


ይህንን የስታርት አፕ ሀሳብን የሚያበረቱ የፖሊሲ ማሻሻያዎችን ሀገሪቱ እንድታደርግ ወትዋች ከነበሩት አካላት መካከል ‘’የኢትዮጵያ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ማህበር’’ የሚጠቀስ ነው፡፡

በኢትዮጵያ የስራ ፈጠራ ስነምህዳር የተመቸ እንዳልሆነ የጠቀሱት የማህበሩ ፕሬዝደንት ሳሚያ አብዱርቃድር፤ በቅርቡ በመንግስት ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት የሚበረታታ ቢሆንም ወደተግባር ለማውረድ ግን አሁንም ብዙ ስራዎች እንደሚቀሩ ለሸገር ተናግረዋል፡፡


በተለይ በተለያየ ጊዜ የታየው የመንግስትም ሆነ የግል መስሪያ ቤቶች የእርስ በእርስ የመነናበብ ችግር ሊቀረፍ እንደሚገባም ጠቅሰዋል፡፡


በኢትዮጵያ የስራ ፈጠራ ሀሳብን በገንዘብ ካለመገደፍ(Idea Financing) በተጨማሪ ዘርፉ የሚመራበት ፖሊሲ መንግስት ሳያዘጋጅ መቆየቱ ዘርፉን እንደጎዳው መንግስት ራሱ አምኗል፡፡


የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) የሚሉትም ይህንኑ ነው፡፡


ማንያዘዋል ጌታሁን


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…


Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw


Youtube: http://tiny.cc/ShegerFM1021Radio


Website: https://www.shegerfm.com/


bottom of page