የኦሞ ኩራዝ ቁጥር ሁለት ስኳር ፋብሪካ ያሉበት ውስብስበ ችግሮች ካልተፈቱለት ለግንባታ የፈጀውን የ341.1 ሚሊዮን ዶላር ብድርን ለመከፍል እንደሚቸገር ፓርላማው አሳሰበ፡፡
- May 4
- 2 min read
ሚያዝያ 26/2018
የኦሞ ኩራዝ ቁጥር ሁለት ስኳር ፋብሪካ ያሉበት ውስብስበ ችግሮች ካልተፈቱለት ለግንባታ የፈጀውን የ341.1 ሚሊዮን ዶላር ብድርን ለመከፍል እንደሚቸገር ፓርላማው አሳሰበ፡፡
በህዝብ ተወካይዎች ምክር ቤት የመንግስት ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የ2018 በጀት ዓመት የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 1፣ 2 እና 3 የስኳር ፋብሪካዎች እና የኦሞ ኩራዝ 5 ፋብሪካ ግንባታ ፕሮጀክትን ተመልክቶ የግብረ መልስ ሪፖርት አሰናድቷል፡፡
በሪፖርቱ መሰረት የኦሞ ኩራዝ ቁጥር ሁለት ስኳር ፋብሪካ የተገነባው በብድር በተወሰደ የ341.1ሚልዮን ዶላር ሲሆን በቀን ፋብሪካው የሚፈጨው የአገዳ መጠን 12 ሺህ ቶን ነው፡፡
ይሁንና ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች በመኖሪያ ቤት፣ በውሃ፣ በባንክና በኢንተርኔት አገልግሎት እጥረት እና በጥቅማጥቅምና በደመወዝ ማነስ ምክንያት ፋብሪካውን ለቀው እየሄዱ በመሆኑ የሚጠበቅበትን ያህል እያመረተ እንዳልሆነ ሪፖርቱ ጠቅሷል፡፡
በተጨማሪም የፋይናንስ አቅርቦት እና የግብዓት አቅርቦትን የመሳሰሉ ከፍተት ችግሮች አሉበት ተብሏል፡፡

በመሆኑም ፋብሪካው ያለበትን የእዳ ጫና ተወጥቶ ትርፋማ እንዲሆን፣ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽንና የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ የተጀመሩ የመስኖና የመብራት ኃይል የሰብስቴሽን ግንባታዎችን በፍጥነት እንዲጠናቀቅ አሳስቧል፡፡
የባለሙያዎችን ፍልሰት ለመግታት የበረሃ አበል፣ የደመወዝ ማሻሻያና መሰረታዊ አገልግሎቶችን ማለትም ውሃ፣ ባንክ፣ ኔትወርክ አገልግቶቶችን ማሟላትም ወሳኝ መሆኑን ቋሚ ኮሚቴው በሪፖርቱ አመላክቷል፡፡
የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 5 ስኳር ፋብሪካ የግንባታ ፕሮጀክት ላይ ባደረገው የመስክ ምልከታም ከፍተኛ የሃበት ብክነት መመልከቱን አረጋግጧል ፡፡
በዚህም ለፋብሪካው ተብለው የተገዙ 75% የሚሆኑ ውድ ማሽነሪዎች ያለምንም መጠለያ በሜዳ ላይ ተበትነው እንደሚገኙ ቋሚ ኮሚቴው ተመልክቻለው ብሏል፡፡
በዚህም ምክንያት ከፍተኛ ወጪ ወጥቶባቸው የተጋዙ ማሽነሪዎች የዝገትና የብልሽት አደጋ እንደተጋረጠባቸው በሪፖርቱ መረጋገጡን ተመልክተናል፡፡
ፕሮጀክቱ ተገቢ የሆነ የቴክኒክና የኢኮኖሚ የአዋጭነት ጥናት ሳይከተል መጀመሩን የጠቀሰው ሪፖርቱ አሁን ላይ የግንባታው ሂደት ሙሉ በሙሉ ተቋርጧል ሲል አስረድቷል፡፡
የፕሮጀክቱን የቀጣይ እጣ ፈንታ ለመወሰን ደግሞ ተገቢውን የቴክኒክ ምርመራ ለማድረግ የዘርፉ ባለሙያዎች ያሉበት ቡድን በማቋቋም በሜዳ ላይ የሚገኙ ማሽነሪዎች አሁን ላይ ያላቸውን የቴክኒክ ብቃትና የጉዳት መጠን በዝርዝር እንዲጠና አሳስቧል፡፡
የፋብሪካውን የአዋጭነት ክለሳ (Feasibility Review) በማካሄድ ፕሮጀክቱን አሁን ባለበት ሁኔታ ማስቀጠል ያለውን ሀገራዊ ፋይዳ እንዲጠናም አክሏል፡፡
ትዕግስት ዘሪሁን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7



Comments