የታህሳስ ወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት 9.7 በመቶ ሆኗል ሲል የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ተናገረ።
- sheger1021fm
- 9 minutes ago
- 1 min read
ጥር 1/2018
የታህሳስ ወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት 9.7 በመቶ ሆኗል ሲል የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ተናገረ።
የታህሳስ 2018 ዓ.ም አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት መጠን 9.7 በመቶ ደርሷል፤ ይህም በታህሳስ 2017 ዓ.ም ከተመዘገበው 17.0 በመቶ ጋር ሲነፃፀር ከፍተኛ ቅናሽ አሳይቷል ሲል ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል።
የወር ከወር አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት በታህሳስ 2018 ዓ.ም በ0.3 በመቶ የቀነሰ ሲሆን፤ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወር ጋር ሲነጻጸር የ0.8 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።
የምግብና አልኮል ያልሆኑ መጠጦች የዋጋ ግሽበት 9.8 በመቶ የደረሰው በዋናነት የአትክልት፣ የሥጋ፣ የስኳር እና የጣፋጭ ምግቦች፣ የወተት ተዋጽኦዎች፣ የፍራፍሬ፣ የዘይትና የቅባት እንዲሁም የሌሎች የምግብ ሸቀጦች ዋጋ በመጨመሩ ነው።

በሌላ በኩል የዳቦ እና የጥራጥሬዎች የዋጋ ግሽበት ባለፈው ወር በነበረበት ደረጃ ቀጥሏል ሲል አስረድቷል።
ምግብ ነክ ያልሆነ የዋጋ ግሽበት 9.6 በመቶ የደረሰ ሲሆን፤ ለዚህም አስተዋፅዖ ያደረጉት ትራንስፖርት (17.6 በመቶ)፣ አልኮል መጠጦችና ትምባሆ (10.4 በመቶ)፣ ኮሚኒኬሸን (13.9 በመቶ)፣ የቤት እቃዎች (12.5 በመቶ)፣ ምግብ ቤቶችና ሆቴሎች (13.8 በመቶ) እንዲሁም ልዩ ልዩ እቃዎችና አገልግሎቶች (21.5 በመቶ) ሆነው ተመዝግበዋል።
ከዓመት ዓመት እና ከወር እስከ ወር ያሉት መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፣ የዋጋ ግሽበቱ ካለፈው ዓመት ጋርሲነጻጸር ቀንሷል ሲል መግለጫው አስረድቷል።
ከታህሳስ 2017 ዓ.ም ጀምሮ አጠቃላይ የዋጋ ግሽበቱ እየቀነሰ መምጣቱ፣ የዋጋ መረጋጋት ትርጉም ባለው መልኩ እየተሻሻለ መሆኑን የሚያሳይ ጠቃሚ ምልክት ነው ሲል የስታትስቲክስ አገልገሎት ጠቅሷል::
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








