ኢትዮጵያ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች ያለባትን እዳ ለማሸጋሸግ ከአበዳሪዎቹ ጋር ስምምነት ላይ መድረሷ ተነግሯል፡፡
- 35 minutes ago
- 1 min read
ሰኔ 22/2018
ኢትዮጵያ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች ያለባትን እዳ ለማሸጋሸግ ከአበዳሪዎቹ ጋር ስምምነት ላይ መድረሷ ተነግሯል፡፡
የ1 ቢሊዮን ዶላር እዳዋን ለማሸጋሸግ ከአበዳሪዎቹ ጋር ያደረገችው ተደጋጋሚ ድርድር ውጤት ሳያመጣ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ እንዲያውም አበዳሪዎቹ ጉዳዩን ወደ ህግ እንወስደዋለን እያሉም እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ከገንዘብ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው ከሰኔ አምስት እስከ 28 ቀን 2026 በተደረገው ዝግ ውይይት የእዳ ሽግሽግ ድርድሩ በመርህ ደረጃ የሰመረ ሆኗል፡፡

በዚህም መሰረት ከ2 አመት በፊት መክፈል ከነበረበት የ1 ቢሊዮን ዶላር እዳ ላይ አበዳሪዎቹ 12 በመቶውን ለመቀነስ ተስማምተዋል፡፡
በዚህም ዋናው እዳ ከ1 ቢሊዮን ዶላር ወደ 880 ሚሊዮን ዶላር ዝቅ እንዲል ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
በሌላ በኩል በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2024 ተከፍሎ ማለቅ የነበረበት ከ99 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወለድም ስምምነቱ ህጋዊ ሆኖ ሲያልቅ በአንድ ጊዜ እንዲከፈል አበዳሪዎቹና ኢትዮጵያ መስማማታቸው ታውቋል፡፡
የአከፋፈል ሁኔታውን በተመለከተም ዋናው እዳ በ4 አመት ውስጥ እ.ኤ.አ እስከ መጭው ሐምሌ 15,2029 ተከፍሎ ያልቃል ተብሏል ፡፡
ኢትዮጵያ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች የወሰደችው የ1 ቢሊዮን ዶላር እዳ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለመገንባት ወስዳው የነበረ መሆኑ ይታወሳል፡፡
የነበረባትን እዳ ለማሸጋሸግ ኢትዮጵያ ከተለያዩ አበዳሪዎቿ ጋር ያደረገችው ድርድር ሰምሮ የቀረው የዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች እዳ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
በመርህ ደረጃ እዳው እንዲሸጋሸግ ስምምነት ላይ በመድረሱም ኢትዮጵያ የተለያዩ ጥቅሞችን አግኝታለች፡፡
ከዋናው እዳ ላይ 120 ሚሊዮን ዶላር ተቀንሶላታል፡፡
በአንዴ መክፈል የነበረባትን ዋናውን እዳ በ4 አመት የጊዜ ማዕቀፍ በሂደት እንድትከፍል ተፈቅዶላታል፡፡
በዚህ መሰረት እስከ ሐምሌ 15,2026 ድረስ 180 ሚሊዮን ዶላር ሌላ 100 ሚሊዮን ዶላር ደግሞ በመጭው አመት ሐምሌ 15፣2027 እንድትከፍል ተስማምተዋል፡፡ እንዲሁም 300 ሚሊዮን ዶላር ሐምሌ 15,2028 እና ቀረውን 300 ሚሊዮን ዶላር ደግሞ ሀምሌ 15,2029 እንድትክፈል በመርህ ደረጃ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ስምምነቱንም IMFን ጨምሮ አለም አቀፍ አበዳሪዎች አልነቀፉትም ተብሏል፡፡
ትዕግሥት ዘሪሁን




Comments