ኢትዮጵያ እና ቻይና ባለፈው ዓመት 8.5 ቢሊዮን ዶላር የንግድ ልውውጥ አድርገዋል፡፡
- 3 hours ago
- 1 min read
ሚያዝያ 20/2018
ኢትዮጵያ እና ቻይና ባለፈው ዓመት 8.5 ቢሊዮን ዶላር የንግድ ልውውጥ አድርገዋል፡፡
ከዚህ ውስጥ 8 ቢሊዮን ዶላሩ ቻይና ወደ ኢትዮጵያ ሸቀጦቿን ልካ ያገኘቺው ገቢ ሲሆን ቀሪው 5 መቶ ሚሊዮን ዶላሩ የኢትዮጵያ ምርቶች በቻይና ገበያ ያወጡት ዋጋ ነው፡፡
በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የንግድ ሚዛን ልዩነቱ እጅግ ሰፊ ነው፡፡
የሁለቱ ሀገራት የንግድ ትስስር የበለጠ እንዲጠብቅ ካደረጉ ማህበራት መካከል የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክርቤት ቀዳሚው እንደሆነ ይነገራል፡፡
የምክር ቤቱ ምክትል ዋና ፀሀፊ አቶ ካሳሁን ማሞ የሁለቱ ሀገራት የንግድ ትስስር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ይናገራሉ፡፡
የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ቻይና ከሚገኙ የተለያዩ የንግድ ማህበራት ጋር የጋራ ስምምነት እየተዋዋለ መሆኑን የነገሩን ሲሆን ከቻይና በዋናነት ወደ ኢትዮጵ እየገቡ ያሉት ግዙፍ የፋብሪካ ማሽነሪዎችና የኤሌክትሮኒክስ ውጤቶች ፣ ለግንባታው ዘርፍ የሚያስፈልጉ ግብአቶች ተጠቃሽ መሆናቸውን ነግረውናል፡፡
ኢትዮጵያ በዓመት ለምታስገባው የገቢ ምርት ወደ 24 ቢሊዮን ዶላር የምታወጣ ሲሆን 8 ቢሊዮን የሚሆነው ከቻይና የሚመጣ የገቢ ምርት ነው፡፡
ታዲያ ኢትዮጵያውያን ነጋዴዎች የህን የንግድ ሚዛን ለማጥበብ ምን እየሰሩ ነው ? የንግድ ምክር ቤቱስ የሚያደርጋቸው ጥረቶች አለ ይሆን ስንል ምክትል ዋና ፀሀፊውን አቶ ካሳሁን ማሞን ጠይቀናቸዋል፡፡
በምላሻቸውም የሚላኩ ምርቶች እሴት እንዲጨመርባቸው ፣ ቻይናውያን ባለሀብቶችም ኢትዮጵያ ውስጥ ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥረት እንደሚያደርጉ ጠቅሰዋል።
አሁን ላይ ከ5,000 በላይ የቻይና ባለሃብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት ስራ ላይ መሰማራታቸውን የነገሩን አቶ ካሳሁን ይህም ቻይናውያኑ እዚሁ ሀገር ቤት ምርቶቻቸውን እንዲያመርቱ ለማድረግና ያለው የንግድ ሚዛን ጉድለቱንም ለማጥበብ ይረዳል ብልዋል፡፡

ይህን ለማድረግም የኢትዮጵ ባለሃብቶችና የቻይና ባለሃብቶች አብረው የሚሰሩበት መንገዶችን እንደሚያመቻቹም አስረድተዋል፡፡
በረከት አካሉ




Comments