ነሀሴ 27 2017 - ውዳሴ ዳያግኖስቲክ ማዕከል በዚህ ዓመትም ከ3,000 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የነፃ ምርመራ አገልግሎት ማሰናዳቱን ተናገረ
- sheger1021fm
- Sep 2
- 1 min read
ላለፉት 15 ዓመታት ጳጉሜን ለጤና በሚል ነፃ የጤና ምርመራ ሲሰጥ የቆየው ውዳሴ ዳያግኖስቲክ ማዕከል በዚህ ዓመትም ከ3,000 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የነፃ ምርመራ አገልግሎት ማሰናዳቱን ተናገረ፡፡
ማዕከሉ ላለፉት ዓመታት የህክምና ውጪያቸውን መሸፈን ላልቻሉ ከ60,000 በላይ ሰዎች ነፃ የምርመራ አገልግሎት መስጠቱን ተናግሯል።
በየዓመቱ ጳጉሜን ለጤና በሚል ማዕከሉ በሚያደርገው ነፃ የምርመራ አገልግሎት በሃኪም ተጨማሪ ምርመራ ታዞላቸው ነገር ግን ከፍለው አገልግሎት ማግኘት ለማይችሉ ሰዎች ከፍተኛ ወጭ የሚጠይቁ የምርመራ ዓይነቶችን በነፃ ሲሰጥ ቆይቷል ተብሏል፡፡
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በመንግስት ከሚሰጡ ነጻ የህክምናና ምርመራ አገልግሎቶች በተጨማሪ እንደዚህ ባሉ የግል ተቋማት የሚሰጡ የምርመራ አገልግሎቶች ማህበረሰብን በመጥቀም በተለይ ከፍለው ለመታከም አቅም የሌላቸውን ሰዎች ለማገዝ አስተዋጽኦ እንዳለው የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ተናግረዋል፡፡

በመንግስት የጤና ተቋማት በተጀመረው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በዚህ ዓመት ከሐምሌ አንድ ጀምሮ ከስድስት ሚሊየን በላይ ሰዎች የነፃ ምርመራና ህክምና አገልግሎት ከሌሎች ደጋፊ ተቋማት ጋር በመሆን መሰጠቱንም ሚኒስትሯ ጠቅሰዋል፡፡
የውዳሴ ዲያግኖስቲክ ማዕከል መስራችና ጄኔራል ማናጀር የሆኑት ወይዘሮ ውዳሴ ዕንቁብርሃን በበኩላቸው ማዕከሉ ጳጉሜን ለጤና በሚል በየአመቱ በሚያካሂደው የነፃ የጤና ምርመራ አገልግሎት ባለፉት 15 ዓመታት ከስልሳ ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች አገልግሎት መስጠቱን እና በዚህ አመትም ተመሳሳይ የተለያዩ የበጎ ፈቃድ ስራዎችን ለመከወን መሰናዳቱን ተናግረዋል፡፡
የማዕከሉን ነፃ የምርመራ አገልግሎት ለማግኘትም በባለሙያ ምርመራ እንደሚያስፈልግ መታዘዝ እንዲሁም ተጠቃሚዎች ከፍለው መታከም እንደማይችሉ ማስረጃ ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል ተብሏል፡፡
ይህንን የሚያሟሉ አገልግሎት ፈላጊዎችም ከነሐሴ 26 - 30 2017 ዓ.ም ድረስ በማዕከሉ አድራሻ 9888 ፣ 0940040404 ፣ 0940050505 በመደወል መመዝገብ እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s











Comments