ነሀሴ 21 2017 - የስታርት አፕ አዋጅ በጤናው ዘርፍ ለሚከወኑ የተሻሻሉና ዘመናዊ አሰራሮችን ለመተግበር ያግዛል ተባለ
- sheger1021fm
- Aug 27
- 1 min read
በቅርቡ የፀደቀውና አዳዲስ የፈጠራ ስራዎችን ያበረታታል የተባለው የስታርት አፕ አዋጅ በጤናው ዘርፍ ለሚከወኑ የተሻሻሉና ዘመናዊ አሰራሮችን ለመተግበር ያግዛል ተባለ፡፡
በጤና ዘርፉ ከሚሰጡ አገልግሎቶችም ስምንቱ በተለይ በኢኖቬሽን የተደገፈ አሰራር እንዲከተሉ እየተደረገ ነው ተብሏል፡፡
በተለያዩ የጤና አገልግሎት መስጫዎች ላይ ዘመናዊ አሰራሮችን ለመከተል እና በተለይም አገልግሎቶችን ከማሻሻል አኳያ የጤና ኢኖቬሽን ላይ ትኩረት ማድረጉን የጤና ሚኒስቴር ተናግሯል፡፡

አቶ ደነቀ አየለ በጤና ሚኒስቴር የጤና ሥርዓት ኢኖቬሽንና ጥራት መሪ ስራ አስፈጻሚ ክፍል አስተባባሪ ናቸው፡፡
በጤናው ዘርፍ የተሻሻለው ፖሊሲ በተለይ ዘመናዊ አሰራሮችን በአገልግሎቱ ላይ መተግባር አንድ የተቀመጠ ግብ በመሆኑ በስፋት እንዲሰራበት ለማድረግ የጀመርናቸው ስራዎች አሉ ብለዋል፡፡
ኢኖቬሽንን በተለያዩ ዘርፎች ለመተግበር ሁለተኛ ዙር ፖሊሲ ወደ ስራ መግባቱን የሚጠቅሱት አቶ ደነቀ በስራው ላይ ያሉትን ሂደቶች በተመለከተ በጤናው ላይ በየጊዜው ግምገማ እንደሚደረግበት ይናገራሉ፡፡
ከጤና አገልግሎቶች ውስጥም ተላላፊ ያልሆኑ ህመሞች፣ የእናቶችና ህፃናት ጤና እና ሌሎች 6 አገልግሎቶች ተለይተው የህክምና እና መከላከል ስራዎችን በዘመናዊ አሰራር ለመደገፍ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር በመሆን እየተተገበሩ ያሉ አሰራሮች አሉ ብለዋል አቶ ደነቀ፡፡
በኢትዮጵያ በቅርብ ዓመታት በጤና ተቋማት ላይ ፈጠራን እንዲሁም የተገልጋዮችን እንግልት እንዲቀንሱ በሚል የተተገበሩ የኢኖቬሽን ስራዎች ከዚህ ቀደም የሚታዩ ችግሮችን እንዲሻሻሉ ማድረጉ ተነግሯል፡፡
ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሚከወኑ የጤናው ዘርፍ አገልግሎቶች ማሻሻያ በተለይ የአገልግሎት ጥራትና ደህንነት ላይ ያሉ ክፍተቶችን ለማስወገድም የሚያግዝ ነው ሲል የጤና ሚኒስቴር ተናግሯል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ….
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
Comments