ባለፉት ጊዜያት በነበረው የ12ኛ ክፍል የተማሪዎች ውጤት ዝቅ ማለት «ተማሪዎች የመማር ፍላጎታቸው እየቀነሰ ነው» የሚል ሀሳብ ሲነሳ ይደመጣል።
- 3 hours ago
- 2 min read
ነሐሴ 14 2018
ባለፉት ጊዜያት በነበረው የ12ኛ ክፍል የተማሪዎች ውጤት ዝቅ ማለት «ተማሪዎች የመማር ፍላጎታቸው እየቀነሰ ነው» የሚል ሀሳብ ሲነሳ ይደመጣል።
በሌላ በኩል ደግሞ ይህ የፈተና ስርዓት ጥብቅ መሆኑ ተማሪዎችን የበለጠ በራሳቸው እንዲተማመኑ እያደረገ ነው የሚል ሃሳብ ከሌላኛው ወገን ይነሳል።
አሁን በመማር ማስተማር ሂደቱ ላይ የሚደረገው ጥብቅ የፈተና ስርዓት እና ወጣቶች የሚጠቀሟቸው ቴክኖሎጂዎች በትምህርት ስርዓቱ ላይ ምን አስተዋፅኦ እያበረከቱ ይሆን? መምህራንን ጠይቀናል።
መምህር ያሬድ አስፋው በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን አስተማሪ ናቸው። «ባለፉት ጊዜያት ለተማሪዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ በተሰጡ ፈተናዎች ውጤት አለማስመዝገባቸው ዋናው ምክንያት መምህራኑ ደካማ በመሆናቸው ነው» ይላሉ።
ጠንካራ መምህር ካለ ተማሪዎችን በአግባቡ ያበቃል የሚሉት መምህሩ፣ ለተማሪ መውደቅም ሆነ መጎበዝ ምክንያት ከሚሆኑት ቀዳሚዎች መካከል አንዱ አስተማሪው እንደሆነ አብስረዋል ።
መምህር አረጋ ዮሴፍ በከምባታ ዞን አስተማሪ ናቸው። እሳቸው በሚያስተምሩበት አካባቢ ያሉ ተማሪዎች ሲማሩ «በትምህርት እለወጣለሁ» ብለው በማመን እንዳልሆነ ያስረዳሉ።
አብዛኛው ተማሪ ወደ ደቡብ አፍሪካ ወይም ወደ አረብ ሀገራት ለመሄድ ውጥን ይዞ እንደሚማርና ትምህርቱንም የሚያየው «ጊዜ ማሳለፊያ» አድርጎ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ይህም የሆነው በትምህርት ኑሮን መለወጥ እንደማይቻል ተማሪዎች ስለሚያምኑ ነው፤ አካባቢው ላይም ብዙ ወጣቶች በስደት ሄደው የቤተሰቦቻቸውን ኑሮ ሲለውጡ ስለሚያዩ የነሱም ህልም ያው ይሆናል ብለዋል።
መምህር ሮቤል ሙልዬ በሰሜን ወሎ አካባቢ አስተማሪ ሲሆኑ፣ ከላይ በተነሱት ሁለቱም ሃሳቦች እንደሚስማሙ ነግረውናል። «ክፍለ ሀገር ላይ አሁን ትምህርት ማስኬድ እጅግ ከባድ እየሆነ ነው» የሚሉት መምህሩ፣ ተማሪው በትምህርት ዘርፍ ላይ ተስፋ እየቆረጠ እንደሆነ አብራርተዋል።
«አሁን ያሉ ቴክኖሎጂዎች ለተማሪው ሁለት እድሎችን ይዘው መጥተዋል» ያሉት መምህሩ፣ በጥሩ ሁኔታ ለሚጠቀምበት የተሻለ እውቀት የሚያገኝበት ሲሆን፣ አለበለዚያ ግን ጊዜውን በማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ በማባከን ሰዓቱን እንደሚጨርስ ጠቅሰዋል ።
በተማሪዎች ውስጥ የሚታየውን ተስፋ መቁረጥ እና «በትምህርት መለወጥ አይቻልም» የሚለውን አስተሳሰብ ለማስቀረት በመምህራን ጥረት ብቻ ሊሳካ እንደማይችል ይናገራሉ።
ወላጆች ለዚህ ትልቅ ሚና መጫወት እንዳለባቸው የጠቆሙት መምህሩ፣ ልጆች ከትምህርት ቤት ከሚያገኙት እውቀት በተጨማሪ መጻሕፍትንና ቴክኖሎጂን አጋዥ አድርገው በመጠቀም የተሻለ ውጤት እንዲያመጡና በትምህርት የበለጠ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ማስረዳት እንደሚያስፈልግ መክረዋል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ.....
በረከት አካሉ
_edited.jpg)



Comments