በከባድ ሙስና የተከሰሱትን ወ/ሮ በረከት ወርቁን ጨምሮ 4 ተከሳሾችን፤ ፖሊስ ፍርድ ቤት ማቅረብ ሳይችል ቀረ፡፡
- 11 hours ago
- 1 min read
ሰኔ 1/2018
በከባድ ሙስና የተከሰሱትን ወ/ሮ በረከት ወርቁን ጨምሮ 4 ተከሳሾችን፤ ፖሊስ ፍርድ ቤት ማቅረብ ሳይችል ቀረ፡፡
በከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸው በፖሊስ የ'ይፈለጋሉ" ማስታወቂያ የወጣባቸው ወ/ሮ በረከት ወርቁን ጨምሮ አራት ተከሳሾን ፖሊስ በዛሬ ፍርድ ቤት እንዲያቀርብ ታዞ ነበር።
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው እንዲቀርቡ በማዘዝ ለሰኔ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 3ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት፤ "በገበያ ላይ የነዳጅ እጥረት እንዲከሰት አድርገዋል" የተባሉ የኢትዮጵያ ነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተርን እና የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ዋና ዳይሬክተርን ጨምሮ በ13 ግለሰቦች ላይ የተመሰረተውን የከባድ ሙስና ወንጀል ክስ፣ የክስ መቃወሚያ እና የአቃቤ ህግን ምላሽ ዛሬ መርምሯል።

የፌደራል አቃቤ ህግ ተከሳሾቹን በዋና ወንጀል አድራጊነት እና በልዩ ተካፋይነት፤ ስልጣንን ያለአግባብ በመገልገልና የመንግስትን ስራ በማይመች አኳኋን በመምራት ወንጀል ከሷቸዋል።
ችሎቱ የተከሳሾችን የክስ መቃወሚያ እና የአቃቤ ህግን ምላሽ ለመስማት ለዛሬ ሰኔ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ቀጠሮ ይዞ የነበረ ቢሆንም፣ በክስ መዝገቡ ከ6ኛ እስከ 10ኛ ተራ ቁጥር ላይ የተጠቀሱት ተከሳሾች ሳይገኙ ቀርተዋል።
ችሎት ያልተገኙት ተጠርጣሪዎች በከባድ የሙስና ወንጀል ተፈልገው ማግኘት ባለመቻሉ፣ ፖሊስ ቀደም ሲል የ"ይፈለጋሉ" ማስታወቂያ አውጥቶባቸው እንደነበር ይታወሳል።
ዛሬ በዋለው ችሎት የቀረበውን የክስ መቃወሚያ እና የአቃቤ ህግን ምላሽ የመረመረው ፍርድ ቤቱ፤ አቃቤ ህግ ክሱን ለይቶ (አሻሽሎ) እንዲያቀርብም አዝዟል።
በተጨማሪም በችሎቱ ያልተገኙት ተከሳሾች በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግላቸው ትዕዛዝ አስተላልፏል።
በመዝገቡ 7ኛ ተከሳሽ የሆኑት ወ/ሮ በረከት ወርቁ ከሀገር መውጣታቸው በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች በሚያደርጉት ንግግር በመረጋገጡ፣ አቃቤ ህግ ለእሳቸው ጥሪው በአዲስ ዘመን እና በኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጦች ጭምር እንዲያወጣ ባቀረበው ማሳሰቢያ መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
ችሎቱ የተሻሻለውን ክስ ለመመልከት እና የጥሪውን ሂደት ለመከታተል ለሰኔ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ገዛ ጌታሁን




Comments