በኢትዮጵያ የአሉሚኒየም ምርቶች ላይ የተሰማራው ''ቴክሃፍ አሉሚኒየም'' አለም አቀፍ የጥራት መስፈርቶችን በማሟላት እውቅና ማግኘቱ ተነገረ
- 1 hour ago
- 1 min read
ሚያዝያ 22/2018
በኢትዮጵያ ለአውሮፕላን ማረፊያዎች፣ የሃይል ማመንጫዎች፣ኢንደስትሪ ፓርኮችና ሌሎችም ግዙፍ የግንባታ ስራዎች የሚውሉ የአሉሚኒየም ምርቶች ላይ የተሰማራው ቴክሃፍ አሉሚኒየም የተባለ ተቋም አለም አቀፍ የጥራት መስፈርቶችን በማሟላት እውቅና ማግኘቱ ተነገረ፡፡
ተቋሙ በቅርቡ ወደ አለም አቀፍ ገበያ እንደሚቀላቀለም ጠቅሷል፡፡
ቴክሃፍ አሉሚኒየም አራት ዓለም አቀፍ የጥራት ምስክር ወረቀቶችን ማግኘቱ የተነገረ ሲሆን እውቅናዎቹ በኢትዮጵያ የተሰሩ ምርቶች በዓለማቀፍ ገበያ ገብተው እንዲወዳደሩ ለማድረግ በር የሚከፍት ነው ተብሏል፡፡
በዓለም ላይ የአሉሚኒም ምርቱ ካለው የምርት እድገት አንጻር የኢትዮጵያ ዝቅተኛ መሆኑን የሚያነሱት የቴክሃፍ አሉሚኒየም የሽያጭ ክፍል ሃላፊ የሆኑት አቶ ጌታሁን ጥላሁን ተቋማቸው ይህንን ክፍተት ለማጥበብና የኢትዮጵያ ምርት ከአለም ገበያ ጋር ተወዳዳሪ እንዲሆን የሚሰራ ነው ብለዋል፡፡
ለአሉሚኒየም ምርት የሚሆኑ አብዛኛዎቹ ግብዓቶች ከውጭ እንደሚገቡ የሚጠቅሱት አቶ ጌታሁን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆንና ምርቶችንም ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የጥሬ እቃ ማምረቻውንም መሳሪያ ጭምር ቴክሃፍ አሉሚኒየም በሀገር ውስጥ እየተከለ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ በአሉሚኒየም ምርት ከሌሎች ሀገራት ጋር ተወዳዳሪ እንድትሆን የተለያዩ አማራጮች እየተጠቀምን ነው የሚሉት የቴክሃፍ አሉሚኒም የሽያጭ ክፍል ሃላፊው ለዚህም አለማቀፍ የጥራት መመዘኛዎችን ማሟላትና ዘመናዊ የምርት ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
ቴክሃፍ አሉሚኒም በ4 ቢልየን ብር መነሻ ካፒታል በትግራይ ክልል መቐለ ከተማ አካባቢ የተገነባ ሲሆን በዓመት ከ15ሺህ ሜትሪክ ቶን በላይ በቀን ደግሞ ከአርባ አምስት ቶን በላይ አሉሚኒየም የሚያመርት ፋብሪካ ነው፡፡
ፋብሪካው በመጪዎቹ ስድስት ወራት የማምረት አቅሙን በእጥፍ በማሳደግ ወደተለያዩ ሀገራት የአሉሚኒየም ምርቶችን ኤክስፖርት ለማድረግ የማስፋፊያ ስራ እየከወነ መሆኑም ሰምተናል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ…..
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7




Comments