በኢትዮጵያ ትምህርት የቻይንኛ ቋንቋን ለማስተማር የሚያስችል የሁለትዮሽ የትብብር ስምምነት መፈረሙ ትምህርት ሚኒስቴር ተናገረ።
- Jun 11
- 1 min read
ሰኔ 4/2018
በኢትዮጵያ ትምህርት የቻይንኛ ቋንቋን ለማስተማር የሚያስችል የሁለትዮሽ የትብብር ስምምነት መፈረሙ ትምህርት ሚኒስቴር ተናገረ።
ስምምነቱን የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታው ክንደያ ገብረሕይወት(ፕ/ር) እና በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቺን ሃይ በጋራ ፈርመውታል ተብሏል።
ስምምነቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የረጅም ጊዜ ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር እና በተለይም በትምህርት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በባህል ልውውጥ ዙሪያ አዳዲስ ምዕራፎችን የሚከፍት ነው ብሏል ትምህርት ሚኒስቴር።

በፊርማ ስነ-ስርዓቱ ላይ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታው ክንደያ ገብረሕይወት(ፕ/ር) ፣ ስምምነቱ ከዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ባለፈ በቱሪዝም፣ በህዝብ ለህዝብ ትስስር እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ሲሉ አስረድተዋል።
"ዜጎቻችን የተለያዩ ቋንቋዎችን እንዲማሩ መደረጉ በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ሆነው እንዲወጡ ትልቅ እድል ይፈጥራል" ሲሉም አክለዋል ሚኒስትር ድኤታው፡፡
በተለይም ቻይና በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ቴክኖሎጂ ዘርፍ የደረሰችበትን የላቀ ደረጃ እና የነፃ የትምህርት ዕድል (Scholarship) ለኢትዮጵያውያን የምታመቻችበትን ሁኔታ ለማሳለጥ ስምምነቱ መሠረት መሆኑን አብራርተዋል።
ስምምነቱ በስርዓተ ትምህርት ዝግጅት፣ በመምህራን ስልጠና እና በቁሳቁስ አቅርቦት ላይ የቴክኒክና የቻይና ቋንቋ መምህራንን ድጋፍ የሚያጠቃልል ሲሆን፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የዕውቀት ልውውጥን እና የስኮላርሺፕ ዕድሎችንም ያሰፋል ተብሏል።
በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቺን ሃይ፤ በአሁኑ ወቅት በቻይና ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የአማርኛ ቋንቋን ማስተማር መጀመሩ የሀገራቱን ታሪካዊ ግንኙነት ይበልጥ ያጠናከረና በባህል ልውውጥ ረገድ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ መሆኑን ተናግረዋል ሲል ትምህርት ሚኒስቴር በማህበራዊ የትስስር ገፁ ላይ አስፍሯል፡፡
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i





Comments