በአንደኛ ደረጃ እና በመካከለኛ ደረጃ ባሉ ትምህርት ቤቶች ላይ የመፅሐፍት እጥረት
- 2 hours ago
- 2 min read
ሚያዝያ 28/2018
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመፅሐፍት እጥረቱ በአንደኛ ደረጃ እና በመካከለኛ ደረጃ ባሉ ትምህርት ቤቶች ላይ ከፍተኛ መሆኑን በተለያዩ ጊዜያት መነገሩ ይታወሳል፡፡
የትምህርት ሚኒስቴርም ይህንን ችግር ለመፍታት በዚህ ዓመት 23 ሚሊዮን የአንደኛ እና የመካከለኛ ደረጃ ትምህርት መማሪያ መፅሐፍት ማሳተሙና ማከፋፈሉን ተነግሯል።
በ2019 የትምህርት ዘመን ይደርሳል የተባለ ደግሞ 36 ሚሊዮን የአንደኛ እና የመካከለኛ ደረጃ ትምህርት መማሪያ መፅሐፍትን ለማሳተም የመጨረሻ ደረጃ ላይ መድረሱን የትምህርት ሚኒስትሩ ብርሃኑ ነጋ(ፕ/ር) አስረድተዋል።
ታዲያ በዚህ ስራ ክልሎች ምን እየሰሩ ነው? የመፅሀፍት እጥረቱስ በምን ሁኔታ እየተወጡት ይሆን ስንል ጠይቀናል፡፡

የአፋር ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሳ አደም (ዶ/ር) በዚህ ዓመት ትምህርት ሚኒስቴር አትሞ ከሰጠው መፅሐፍት በተጨማሪ በራሱ በጀትምት ክልሉ በማሳተም ማሰራጨቱን ነግረውናል፡፡
ይህም ሆኖ ችግሩ አንድ መፅሐፍ ለአንድ ተማሪ ማዳረስ ያልተቻለባቸው የትምህርት አይነቶች መኖራቸውን ያስረዳሉ፡፡
የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ቶላ በሪሶ(ዶ/ር) በኦሮሚያ ክልል በአንደኛ ደረጃ እና በመካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያለው የተማሪ ቁጥርና የመፅሀፍ አቅርቦቱ የተመጣጠነ አይደለም ብለዋል፡፡

በዚህ ዓመት ትምህርት ሚኒስቴር 5 ሚሊዮን መፅሀፍት ለክልሉ አትሞ መስጠቱን የተናገሩ ሲሆን በመጪው ዓመት ታትሞ ይደርሳል የተባለው መፅሀፍ ለተማሪዎች ማቅረብ ሲቻል ተማሪዎች የተሻለ መፅሐፍት ማግኘት ይችላሉ ሲሉም አስረድተዋል፡፡
የደቡብ ኢትዮጵ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አብዮት ደምሴ የሁለተኛ ደረጃ መፅሀፍት በአብዛኛው ትምህርት ቤቶች ላሉ ተማሪዎች አንድ መፅሀፍ ለአንድ ተማሪ ተዳርሷል ይላሉ፡፡

ከዚያ በታች ባሉ ትምህርትቤቶች ግን የመፅሐፍት እጥረት አለ፤ ይህንን ለመቅረፍም ትምህርት ሚኒስቴር እገዛ እያደረገ ነው ያሉ ሲሆን ክልሉም ከትምህርት ሚኒስቴር በተጨማሪ የራሱ በጀት እየመደበ የመፅሐፍት ህትመቶችን በራሱ አቅም በማሳተምም ለማዳረስ እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
የትምህርት ሚኒስቴር አሁን አሳትሜ ለክክሎች አከፋፍላለሁ ያለው 36 ሚሊዮን የአንደኛ እና የመካከለኛ ደረጃ መማሪያ መፅሀፍት ታትመው ሲከፋፈል የመፅሀፍት ተማሪ ጥምርታው በአብዛኛው የትምህርት አይነት አንድ ለአንድ ይሆናል ተብሏል፡፡
ሙሉውን ለማድመጥ…
በረከት አካሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7





Comments