በምርጫ ወቅት "በታንዛኒያ እና በዩጋንዳ "ላይ የተስተዋለው የኢንተርኔት ገደብ ወይም እቀባ በኢትዮጵያ እንዳይኖር የአፍሪካ ህብረትን ጨምሮ ሌሎች ተቋማት ምክረ ሃሳብ ማቅረባቸውን ተናገሩ።
- 14 hours ago
- 2 min read
ግንቦት 12/2018
በምርጫ ወቅት "በታንዛኒያ እና በዩጋንዳ "ላይ የተስተዋለው የኢንተርኔት ገደብ ወይም እቀባ በኢትዮጵያ እንዳይኖር የአፍሪካ ህብረትን ጨምሮ ሌሎች ተቋማት ምክረ ሃሳብ ማቅረባቸውን ተናገሩ።
የአፍሪካ ህብረት ምርጫውን ለመታዘብ በቂ ዝግጅት ማድረጉን እና የምርጮ ቦርድ ውሳኔን በመጠበቅ ላይ እንደሚገኝ አስረድቷል።
ይህ የተነገረው ግንቦት 10 ቀን 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ድርጅቶች ህብረት ፓራዳይም ኢንሼቲቭ ከተሰኘ መንግስታዊ ካለሆነ ተቋም ጋር በመሆን በዲጂታል መብት ላይ ባሰናዳው ወይይት ላይ ነው።

በራዲሰን ብሉ (Radison blue) ሆቴል በተካሄደው ውይይቱ ላይ የአፍሪካ ህብረት፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት የሳይንስ የባህል ተቋም ዩኔስኮ ፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ፣ የኢትዮ ቴሌኮም ፣ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እና የሌሎች ተቋማት እና ማህበራት ተወካዮች ተገኝተዋል።
የምርጫ ወቅት ከፍተኛ መረጃ የሚመነጭበት እና ልውውጥ የሚደረግብት ስለሆነ ለዚህ የሚያግዝ ጥራት ያለው ኢንተርኔት ተደራሽ ማድረግ እንደሚያስፈልግ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ድርጅቶች ህብረት ዳይሬክተር አቶ መሱድ ገብየሁ አሳስበዋል፡፡
ጥራት ያለው ኢንተርኔት ተደራሽ ማድረግ ምርጫው ተዓማኒ እንዲሆን ከማድረግ ባለፈ የዜጎችን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን መጠበቅ ጭምር መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
አቶ መሱድ ጥራት ያለው ኢንተርኔት ከማድረስ በተጨማሪ የተዛባ እና ሃሰተኛ መረጃን ቁጥጥር የሚደረግበትን መላ መፈለግ እንደሚያስፈልግም አስረድተዋል፡፡

በተጨማሪም የኢንተርኔት መቆራረጥ "በአንዳንድ አካባቢዎች " ባለፈው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ላይ መከሰቱን ያስታወሱት አቶ መሱድ ያለፈው ችግር በአሁኑ 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ላይ እንዳይደገም ሊደረግ ይገባል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበራት ድርጅቶች ህብረት ለምርጫ የሚዲያ ክትትል ሀላፊ እና የውይይቱ ተሳታፊ ነዋል አቡበከር ጥራት ያለው ኢንተርኔት ዜጎች በምርጫ ወቅት ለሚወስኑት ውሳኔ በቂ መረጃ እንዲኖራቸው ስለሚያግዝ ጥራት ያለው ኢንተርኔት ተደራሽ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ተናግራለች፡፡

በውይይቱ ላይ ከአፍሪካ ህብረት ተወክለው የተሳተፉት አቶ ደመቀ ተስፋዬ ከ4 ወር በፊት የቅድመ ምርጫ ሂደት ትንተና ህብረቱ መስራቱን አስረድተዋል፡፡
በዚህም ቡድን ተዋቅሮ ጉዳዩ ከሚመለከተው አካል ጋርም ምርጫው ውጤታማ መሆን በሚችለብት ጉዳይ ህብረቱ መነጋገሩን ተናግረዋል፡፡

የአፍሪካ ህብረት በታዘበው የዩጋንዳ እና ታንዛኒያ ምርጫ ላይ የነበረው የኢንተርኔት መጥፋት በኢትዮጵያ ላይ እንዳይከሰት ከሚመለከታቸው ጋር በቂ ንግግር ማድረጉን አቶ ደመቀ ተስፋዬ አብራርተዋል፡፡
ህብረቱ 7ኛውን አገራዊ ምርጫ ለመታዘብ ዝግጅት ማጠናቀቁንም የተናገሩት አቶ ደመቀ በሌሎች የአፍሪካ አገራት የተስተዋለው የኢንትርኔት መቆራረጥ እንዳይከሰትም ምከረ ሃሳብ ሰጥተናል ብለዋል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ….
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7




Comments