ሰኔ 9 2017 - ህክምናዎችን በድምፅ በመታገዝ መስራት የሚያስችል AI የተገጠመለት የህክምና ማዕከል ስራ መጀመሩን ተናገረ
- sheger1021fm
- Jun 16
- 1 min read
ህክምናዎችን በድምፅ በመታገዝ መስራት የሚያስችል AI የተገጠመለት የህክምና ማዕከል ስራ መጀመሩን ተናገረ ።
በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመረቀው የቤተ ሳይዳ አሜሪካን ሜዲካል ፕላዛ ለህክምና ወደ ውጭ ሀገራት የሚደረግ ጉዞን በእጅጉ የሚያስቀር ነው ተብሎለታል።
የህክምና ማዕከሉ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የታገዘ፤ በኢትዮዽያ የመጀመሪያው የአጥንት መሳሳት መመርመሪያ እና የልብ፣ የአንጎል እና በሰውነት ላይ የሚከሰቱ የደም ስር ችግሮችን ያለ ቀዶ ህክምና መስራት የሚያስችል በድምጽ መታዘዝ የሚችል መሆኑ ልዩ እንደሚያደርገው ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናግረዋል።
በውጭ ሃገር ባለሃብት የተገነባው ''ቤተ ሳይዳ አሜሪካን ሜዲካል ፕላዛ'' በአጠቃላይ 25 ሚሊዮን ዶላር ( 3.5 ቢሊዮን ብር ) እንደወጣበትም ተነግሯል።
ማዕከሉ ዘመኑ የሚጠይቀውን ቴክኖሎጂ ታጥቋል ሲባል 3ኛ እና 4ኛ ደረጃ ላይ ያሉ ከፍተኛ ህክምናዎችን ለመስጠት የሚያስችለው ነው ሲሉ የማዕከሉ ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶክተር አየለ ተሾመ ነግረውናል።
"በውጭ ሀገር የሚደረግ ህክምና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ በመሆኑ ይህንን ለማስቀረት እኛ መሳሪያዎቹን ወደ ሃገር ቤት አምጥተናል፤ በተለይም የልብ፣ የኩላሊት፣ የአጥንት፣ የጭንቅላት፣ የጉበትና ሌሎችም ህክምናዎችን በዚህ መንገድ እንሰጣለን" ብለውናል።
በዋጋ ደረጃም ይህ የህክምና ማዕከል በመደበኛነት በየህክምና ማዕከሉ ከሚጠየቀው ዋጋ በ25 በመቶ የቀነሰ ነው ሲሉ ዋና ስራ አስፈፃሚው አስረድተዋል።

በሃገር ውስጥ አይቻልም ተብለው ወደ ውጭ ሃገራት የሚላኩ የህክምና አገልግሎቶች ሁሉም አሉ ያሉት ስራ አስፈፃሚው ዶክተር አየለ ሆስፒታሉ በሚችለው አቅም አገልግሎት ይሰጣል ብለዋል።
ይሁንና ኢትዮጵያ ትልቅ ሃገር እንደመሆኗ በአንድ ተቋም ሁሉንም ፍላጎት ማሟላት ስለማይቻል መሰል ተቋማት እንደሚያስፈልጓት ጠቅሰዋል።
የህክምና ተቋሙ በሚቀጥለው ዓመት እሰራዋለሁ ባለው የማስፋፊያ ስራ የህክምና ኮሌጅ፣ የልህቀት ማዕከልና የካንሰር ማዕከል እንደሚገነባ ተናግሯል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርም የሜዲካል ቱሪዝምን ለማበርታት ቤተ ሳይዳ አሜሪካን ሜዲካል ፕላዛን ሲያግዝ መቆየቱንና በሚጠየቀው ሁሉ እንደሚያግዝ ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስረድተዋል።
ምንታምር ፀጋው








