መስከረም 28 2018 - አዲሱ የተሸከርካሪዎች መለያ ሰሌዳ አሰጣጥ ስርዓት ታዋቂ ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች በሚፈልጉት መልክ እንዲታተምላቸው የሚፈቅድ ነው ተባለ
- sheger1021fm
- Oct 8
- 2 min read
ዛሬ ይፋ የተደረገው አዲሱ የተሸከርካሪዎች መለያ ሰሌዳ አሰጣጥ ስርዓት ታዋቂ ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች በሚፈልጉት መልክ እንዲታተምላቸው የሚፈቅድ ነው ተባለ፡፡
ይህን ያለው የትራንስፖርት እና ሎጂስቲከስ ሚኒስቴር ነው፡፡
በርካታ ችግሮች ነበሩበት የተባለው የተሸከርካሪ መለያ ሰሌዳ ተቀይሯል፡፡
ጉዳዩን አስመልክቶ መግለጫ የሰጠው የትራንስፖርት እና ሎጂስቲከስ ሚኒስቴር፤ አሁን በስራ ላይ ያለው መለያ ሰሌዳ ከ1994 ጀምሮ ላለፉት 23 ዓመታት በስራ ላይ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡
ሰሌዳው መቀየር አስፈላጊ የሆነበትን ዝርዝር ምክንያቶች ያስረዱት የትራንስፖርት እና ሎጂስቲከስ ሚኒስቴር ሚኒስትር አለሙ ስሜ፤ በቀድሞው የትራንስፖርት አዋጅ መሰረት ሲሰጡ የነበሩት የሰሌዳ ዓይነት፣ አመራረት እና አወጋገድ ወቅቱ ከሚጠይቀው የአገልግሎት አሰጣጥ ጋር አብሮ ስለማይሄድ ነው ብለዋል፡፡

አገልግሎት አሰጣጡ ከዘርፉ እደገት ጋር እንዳልተጣጣመ የተናገሩት ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ተቀብላ ካጸደቀቻቸው አለም አቀፍ ህጎች ጋርም አብሮ እንደማይሄድ አስረድተዋል፡፡
አዲሱ ሰሌዳ ግን የተገልጋዩን እርካታ የሚያረጋግጥ፣ አለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት ያደርገ፣ አሰባሳቢ ወይም የውል ትርክቶችን በሚፈጥር መልኩ የተዘጋጀ ነው ሲሉ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲከስ ሚኒስቴር ሚኒስትር አለሙ ስሜ ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም አዲሱ ሰሌዳ የተሸከርካሪ ሰሌዳ አመራረት፣ አወጋገድ፣ ስርጭት እና ወጥነቱ በቴክኖሎጂ የተደገፈ እንደሆነም ተነግሯል፡፡
አዲሱ መለያ ሰሌዳ በሀገር አቀፍ ደረጃ ወጥ ሲሆን ይህም ከዚህ ቀደም አንድ ተሸከርካሪ ከሌላ አካባቢ ነው የመጣው በሚል የሚፈጸምበትን መድሎ የሚያስቀር ነው ተብሏል።
በቅርቡ ወደስራ በሚገባው የተሽከርካሪዎች የመለያ ቁጥር ሰሌዳ ዓይነቶች እና ምልክቶች መወሰኛ እና የአገልግሎት አሰጣጥ መመሪያ መሠረት " #ታዋቂ_ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች በሚፈልጉት #ድርጅት ስም ወይም አይነት " ሰሌዳ እንዲታተምላቸው ይፈቅዳል ሲሉ ሚኒስትር አለሙ ስሜ ተናግረዋል፡፡

በአዲሱ በተሸከርካሪ ሰሌዳ ላይ ለህግ አስከባሪው ብቻ የሚታይ ተሸከርካሪው የት እንደተመዘገበ፣ የማን እንደሆነ፣ ተሸከርካሪው የተመረተበት ዓመት ፣ በሚስጥር በሰሌዳው ላይ እንደሚታተም የተናገረው ሚኒስቴሩ አዲሱ ሰሌዳ ከዚህ ቀደም በስራ ላይ እንዳለው በብሎን በየጊዜው የሚፈታና የሚታሰር አይደለም ብሏል፡፡
በስራ ላይ ባለው ሰሌዳ መሰረት በኢትዮጵያ ከ1.6 ሚሊዮን በላይ ተሸከርካሪ እንዳለት ተነግሯል፡፡
በመጪዎቹ በሁለት ወራት ውስጥ የቀድሞውን መለያ ሰሌዳ በአዲሱን መቀየር ይጀመራል የተባለ ሲሆን አስካሁን ሁለት ሚሊዮን አዲስ ሰሌዳ ህትመት ታዝዟል ተባሏል፡፡
በተያዘው አዲስ ዓመትም ሙሉ በሙሉ የሰሌዳ መቀየር ስራ እንደሚሰራ ሰምተናል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
🌐Website፡ https://www.shegerfm.com/
🎥YouTube https://tinyurl.com/37tux478
🟦Telegram https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📘Facebook፡ https://tinyurl.com/4tx8t8wm
💬WhatsApp ፡ https://tinyurl.com/ycxjmm3s
👔LinkedIn ፡ https://tinyurl.com/tyfaekvx












Comments