ሐምሌ 7 2017 የውጪ ሀገራት ወሬዎች
- sheger1021fm
- 1 day ago
- 1 min read

የሩሲያ ጦር በምስራቃዊ ዩክሬይን ዳኔስክ ግዛት በኩል ወደ ድኔፕሮ ፔትሮቭስክ ግዛት እየተጠጋሁ ነው አለ፡፡
ጦሩ በሁለቱ ግዛቶች ወሰን ላይ የሚገኘውን ማይረን የተባለ አካባቢ መያዙን እወቁልኝ ማለቱን AFP ፅፏል፡፡
ጦሩ የዩክሬይንን ሰራዊት መከላከያ ሰብሬበታለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡
ከቅርብ ወራት ወዲህ የሩሲያ ጦር ከሚፈፅመው የሚሳየል እና የድሮን ጥቃት በተጨማሪ በምስራቃዊ ዩክሬይን የተለያዩ ስፍራዎች ወደፊት እየገፋ ነው ተብሏል፡፡
አሜሪካ በዩክሬይን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ አጠቃላይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ብትጠይቅም በሩሲያ በኩል ጥያቄው ተቀባይት እንዳላገኘ ይነገራል፡፡
የዩክይሬኑ ጦርነት ከ3 ዓመት ከ4 ወራት በላይ ሆኖታል፡፡

በስፔኗ ቶሬ ፓቼኮ ከተማ በስደተኞች እና በስደተኛ ጠል ቀኝ አክራሪ ቡድኖች አባላት መካከል ከፍተኛ አምባጓሮ ተቀስቅሶ ነበር ተባለ፡፡
ከየትኞቹ ወገን እንደሆነ በግልፅ ባይጠቀስም በአምስት ሰዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን ሬውተርስ ፅፏል፡፡
ማንነታቸው በግልፅ ያልተለየ ስደተኞች ባለፈው ሳምንት አጋማሽ በአንድ ስፔናዊ አዛውንት ላይ ጥቃት አድርሰዋል መባሉ ለቅዳሜ እለቱ አምባጋሮ መጋጋል በምክንያትነት እየተነሳ ነው፡፡
የስፔን መንግስት የቅዳሜውን ረብሻ ተከትሎ በከተማዋ በብዛት የፀጥታ አስባሪዎችን ማሰማራቱ ታውቋል፡፡
በከተማዋ በርከት ያሉ መነሻቸው ከሰሜን አፍሪካ የአረብ አገሮች የሆነ ስደተኞች ይኖራሉ፡፡
አብዛኞቹም በከተማዋ አቅራቢያ ባሉ የእርሻ ስፍራዎች በቀን ሰራተኛነት እንደሚተዳደሩ መረጃው አስታውሷል፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.cocxjmm3s
Comments