600 ሚሊዮን አፍሪካዊያን አሁን ድረስ የኤሌክትሪክ ብርሃን ማየት እንዳልቻሉ የአፍሪካ ህብረት ተናገረ።
- sheger1021fm
- 4 hours ago
- 1 min read
ህዳር 24 2018
600 ሚሊዮን አፍሪካዊያን አሁን ድረስ የኤሌክትሪክ ብርሃን ማየት እንዳልቻሉ የአፍሪካ ህብረት ተናገረ።
ባለው የተደራሽነት ችግር ምክንያት 1 ቢሊዮን ገደማ አፍሪካዊያን ምግባቸውን የሚያበስሉት ንፅህናውን ባልጠበቀ እና ባህላዊ በሆነ መንገድ ነውም ተብሏል።
ይህ የተባለው ፊታችን ታህሳስ 1 እና 2 2018 ዓ.ም የሚካሄደውን የአፍሪካ ኢነርጂ ብቃት ጉባኤን በተመለከተ ለጋዜጠኞች መግለጫ በተሰጠበት ወቅት ነው።

መግለጫውን የሰጡት በአፍሪካ ህብረት የመሰረተ ልማትና ኢነርጂ ኮሚሽነር የሆኑት ሌራቶ ማታቦጌ፤ አፍሪካ ኤሌክትሪክን ለህዝቧ ለማዳረስ ገና ብዙ ስራዎች ይጠብቋታል ብለዋል።
የጉባኤው አላማ የህብረቱ አባል ሃገራት በኤነርጂው ዘርፍ ያላቸውን ተሞክሮ የሚጋሩበት፣ በየሃገራቱ ያሉ የኤነርጂ ብቃትና ቁጠባ ስትራቴጂዎች አተገባበር፣ያሉ ችግሮች ላይ በመነጋገር በዘርፉ የተሻለ ውጤት ካላቸው ልምድ ሚወሰድበት ነውም ብለዋል።
በኤነርጂው ዘርፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው የሚካሄደው በተባለው በዚህ ጉባኤ ኢትዮጵያም በኤነርጂ መሰረተ ልማት የተሻለ የፋይናንስ ሞዴል ካላቸው የአፍሪካ ሃገራት ልምድ በመውሰድ በዘርፉ የምትከተለውን ፖሊሲ እንድትፈትሽ እድል ይፈጥርላታል ያሉት የኢትዮጵያ ነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ባህሩ ኦልጂራ ናቸው።
ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት ፕሮግራም ተቀርጾ እየተሰራ መሆኑን ተናግረው፤ ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል አቅም እንዳላትና በምስራቅ አፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል ለመሆን እየሰራች እንደምትገኝም ጠቁመዋል።
በሚቀጥለው ሳምንት በሚካሄደው በዚህ የኤነርጂ ብቃት ላይ ባተኮረው ጉባኤ ከ400 በላይ የዘርፉ ተዋንያን ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል መባሉን ሰምተናል።
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
👇👇👇
🌐Website፡ https://www.shegerfm.com/
🎥YouTube https://tinyurl.com/37tux478
🟦Telegram https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📘Facebook፡ https://tinyurl.com/4tx8t8wm
💬WhatsApp https://tinyurl.com/ycxjmm3s








