ጥር 29፣2017 - ''የውጭ ሀገር የስራ ስምሪት ዕድሉን እናገኛለን ብለን ወደ አዲስ አበባ መጥተን፤ ጎዳና እስከ መውጣት ደርሰናል''
- sheger1021fm
- Feb 7
- 1 min read
የመንግስትን ጥሪ ተቀብለን የውጭ ሀገር የስራ ስምሪት ዕድሉን እናገኛለን ብለን ወደ አዲስ አበባ መጥተን፤ ጎዳና እስከ መውጣት ደርሰናል ሲሉ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች የመጡ ወጣቶች ተናገሩ፡፡
ወጣቶቹ መንግስት ያወጣውን አዋጅ ተከትሎ በስራ እና ክህሎት ሚኒስቴር በኩል የሚሰጠውን ስልጠና መውሰዳቸውንና አስፈላጊውን ሰርተፍኬት እንደተሰጣቸውም ተናግረዋል።
በነፃ ነው ተብሎ የሚነገርለት ይህ ስልጠና እስከ ስድስት ሺህ ብር መክፈላቸውን አስረድተዋል፡፡
ይሁንና እዚህ መጥተው ስልጠናውን አጠናቀው ፈተናውንም አልፈው ትሄዳላችሁ የተባሉት የውጭ ሃገር ስራ ስምሪት የውሃ ሽታ እንደሆነባቸውም ሰምተናል።

ያለንን ገንዘብ ለስልጠናና ለተለያዩ ወጪዎች በማውጣታችን ባዶ እጃችንን ቀርተናል ወደ የቤተሰቦቻችን ለመመለስ ተቸግረናል ብለዋል።
የስራና ክህሎት መስሪያ ቤት በመሄድ ምንድነው መፍትሄው ብንላቸውም ወደ ኤጀንሲው ሂዱ ይሉናል፤ ወደ ኤጀንሲው ስንሄድ ደግሞ የእናንተ የወንዶቹ ጉዳይ አልተጀመረን በማለት በመሃል ቤት እኛ ለስቃይ ተዳርገናል ሲሉ ወጣቶቹ ነግረውናል።
ወደ ውጪ ሀገር ሰራተኞችን የሚልኩ ኤጀንሲዎች ፌዴሬሽን በበኩሉ የሰለጠነ ሁሉ አይሄድም ብሏል፡፡
የስራ እና ክህሎት ሚኒስቴር ለቀረበው ቅሬታ መልስ አልሰጠም፡፡
ማርታ በቀለ
Comments