ግንቦት 13 2017 - የምርጫ ቦርድ የስራ የአመራር ቦርድ እጩ አባላት መልማይ ኮሚቴ 6 እጩዎችን ለጠ/ሚ ሊያቀርብ መሆኑን ተናገረ
- sheger1021fm
- 5 hours ago
- 1 min read
የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የስራ የአመራር ቦርድ እጩ አባላት መልማይ ኮሚቴ ስድስት እጩዎችን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊያቀርብ መሆኑን ተናገረ፡፡
ኮሚቴው ይህን ያለው የመጨረሻ መግለጫውን በዛሬው እለት ለጋዜጠኞች በሰጠበት ወቅት ነው፡፡
የመልማዩ ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ታጋይ ታደለ በሰጡት መግለጫ የምርጫ ቦርድ የስራ አመራር ምርመላ ሂደት 21 ቀን የፈጀ እንደሆነ ተናግረው በዚህም መሰረት 168 የእጩ ጥቆማዎችን በስልክ በኢሜይል፣ በፖስታ እና በአካል መቀበሉን አብራርተዋል፡፡
ከቀረቡት 168 እጩ ምልምሎች ውስጥ በሶስት መስፈርት ስድስት እጩ ምልምሎች ማለፋቸውን ኮሚቴው አስረድቷል፡፡
በዚህም መሰረት አቶ ተስፋዬ ነዋይ፣ አቶ ተክሊት ይመስል፣ ወ/ሮ ነሲም አሊ፣ ወ/ሮ ዳሮ ጀማል፣ ወ/ሮ ፍሬህይወት ግር ፣ ያሬድ ሀ/ማርያም(ዶ/ር) የምርጫ ቦርድ የስራ አመራር ቦርድ እጩ አባላት ሆነው ቀርበዋል ተብሏል፡፡
ኮሚቴው የሶስት ወንድና የሶስት ሴት እጩ ምልምሎችን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚያቀርብ የተነገረ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩም ከዚህ ቀደም የአገለግሎት ጊዜያቸው ባበቃው ቦርድ አባላት ሶስቱን ይሾማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኮሚቴው በዛሬው መግለጫው ስድስት እጩዎች የተመረጡት ፍትሃዊና በትምህርት ዝግጅታቸው፣ በቃለ መጠይቅ፣ በስራ ልምዳቸው እንዲሁም በፖለቲካ ገለልተኝነታቸው ተመዝነው እንደሆነ የኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ታጋይ ታደለ ተናግረዋል፡፡
የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የስራ አመራር ቦርድ እጩ አባላት መልማይ ኮሚቴ መጋቢት 17 ቀን 2017 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሰይሞ ስራ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://shorturl.at/21bFN