የኢትዮጵያ አጠቃላይ ብድር 51.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን የገንዘብ ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል፡፡
- 27 minutes ago
- 1 min read
ግንቦት 17/2018
የኢትዮጵያ አጠቃላይ ብድር 51.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን የገንዘብ ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል፡፡
ከመካከሉ ከ33 ቢሊዮን ዶላር በላዩ የውጭ እዳ ሲሆን 18.3 ቢሊዮን ዶላሩ ደግሞ ከሃገር ውስጥ የተወሰደ ብድር ነው፡፡
ለመሆኑ የኢትዮጵያ አጠቃላይ ብድር ከሌሎች አገራት አንፃር ሲታይ ከፍተኛ ፣ መካከለኛ ወይስ ዝቅተኛ ?
ሀገሪቱ አሁን ያለችበት የኢኮኖሚ አቅምስ ያለባትን እዳ ለመክፈል የሚያስችላት ይሆን?
የምጣኔ ሃብት በለሞያ የሆኑት አቶ ክቡር ገና የኢትዮጵያ እዳ ከሌሎች አገራት ጋር ሲተያይ ከፍተኛ የሚባል እንዳልሆነ ጠቅሰው የመክፈል አቅሟ ግን "በጣም ደካማ ስለሆነ ጫናው በጣም ከፍ ብሎ ይታያል፣ ለመክፈልም አስቸጋሪ ነው ይላሉ፡፡
የአገር ውስጥ እዳው በኢትዮጵያ ብር ሲመለስ ወደ 3 ትሪሊዮን እንደሚሆን እንዲሁም የውጭ ብድሩ ደግሞ 6 ትሪሊዮን ብር ነው የሚሉት ባለሙያው የውጪ እዳን ለመክፍል የሚያስችል ስራ መሰራት እንዳለበት መክረዋል፡፡
ለምሳሌ አሁን በአገሪቱ ያሉ የሰላም እጦቶች መፈታት እንዳለባቸው ፣ ወደ ውጭ ተልከው የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ የኢንዱስትሪ እና ግብርና ምርቶችን ማሳደግ እንዲሁም በእዳ የተገነቡ ፕሮጀክቶችን ወደ ምርት እንዲገቡ ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ሌላው የምጣኔ ሃብት በለሙያ ቆስጠንጢኒዮስ በረኽ ተስፋ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ አጠቃላይ ብድር ከሌሎች አገራት አንፃር ሲታይ ከፍተኛ የሚባል እንዳልሆነ ጠቅሰው ለብድሩ መከማቸት ግን በእዳው የተሰሩ ፕሮጀክቶች ውጤታማ ባለመሆናቸው እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡
ቆስጠንጢኒዮስ በረኽ ተስፋ (ዶ/ር) ለኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ ለስኳር ፋብሪካዎች፣ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማስፋፊያ እንዲሁም ለመሰል ፕሮጀክቶች እና መሰረተ ልማቶች ኢትዮጵያ ከፍተኛ ገንዘብ መበደሯን ይህም የእዳ ጫናዋን እንዳበረታው ተናግረዋል፡፡
እነዚህ ፕሮጀክቶች ደግሞ ተጠናቅቀው ወደ ምርት በሚፈለገው ደረጃ አለመግባታቸው ኢትዮጵያ ያላትን ውስን የውጭ ምንዛሪ እንዲሻማት አድርጓል ሲሉ ያስረዳሉ፡፡
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ…
ያሬድ እንዳሻው





Comments