ታህሳስ 11፣2017 - በአዲስ አበባና በሸገር ከተማ አዋሳኝ ቦታዎች የመሬት ወረራና ህገወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር መኖሩ ተነገረ
- sheger1021fm
- Dec 20, 2024
- 2 min read
በአዲስ አበባ ከተማና በሸገር ከተማ አዋሳኝ ቦታዎች የሽብር ቡድኖች እንቅስቃሴ፣የመሬት ወረራ፣ህገወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውርና የኮንትሮባንድ ንግድ መኖሩ ተነገረ፡፡
ይህንን ያለው የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ነው፡፡
ቢሮው እነዚህንና ተያያዥ ህገ ወጥ ተግባራት በጋራ ለመቆጣጠር የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ከሸገር ከተማ ጋር ተፈራርሟል፡፡
የከተማዋ #ሰላምና_ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ የሸገር ከተማ ከተቋቋመበት ካለፈው 2015 ዓ.ም ጀምሮ በሰላምና ፀጥታ እንዲሁም ህገወጥ ንግድን ለመቆጣጠር ተመሳሳይ የመግባቢያስምምነት ተፈራርሞ ሲሰራ መቆየቱን ተናግሯል፡፡
ይሁንና ስራውን አጠንክሮ ለማስቀጠል ሌላ ስምምነት ማድረግ በማስፈለጉ በኢሊሌ ሆቴል በተሰናዳው መርሃ ግብር ስምምነቱ ተፈርሟል፡፡
በዚህም ወቅት ባለፉት ሁለት ዓመታት የተሰሩ ስራዎችን ሪፖርት ያቀረቡት በ#አዲስ_አበባ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ የኦፕሬሽን ዘርፍ ዋና ዳይሬክተር ኮማንደር ሙሉጌታ በጋሻው፤ በተለይ በሰላምና ፀጥታ ዙሪያ ሁለቱ ከተማ አስተዳድሮች በሰሯቸው ጠንከር ያሉ ስራዎች በቀደሙት ጊዜያት የነበሩት የፀጥታ ችግሮች ተወግደው ከ2015 ዓ.ም ወዲህ ሃይማኖታዊና ህዝባዊ የአደባባይ በዓላት በሰላም መከበራቸውን ተናግረዋል፡፡
ይሁንና አሁንም በሁለቱ ከተሞች አዋሳኝ ቦታዎች የሽብር ቡድኖች እንቅስቃሴ፣ የመሬት ወረራ፣ ህገወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውርና የኮንትሮባንድ ንግድ በስፋት መኖሩ ጠቅሰው በዚህ ስምምነት እነዚህን ችግሮች ለመቆጣጠር እንሰራለን ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በሁለቱ ከተማ አስተዳድሮች እዚህና እዚያ እያሉ የኢኮኖሚ አሻጥር የሚፈጥሩ ነጋዴዎች መኖራቸውን የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሃላፊ ወ/ሮ ሊዲያ ግርማ ተናግረዋል፡፡
በተለይ በአዲስ አበባ በቅርቡ የተጀመረውን የደረሰኝ ግብይት ቁጥጥር ተከትሎ ሸቀጦችን ከአዲስ አበባ ወደ #ሸገር_ከተማ በማሸሽና በማከማቸት በገበያው ላይ የሸቀጦች እጥረት የሚፈጥሩ አስመጪና ላኪ ነጋዴዎች አሉ ያሉት ሃላፊዋ፤ ይህንን ስርዓት የማስያዝ ስራዎች በጋራ እንደሚሰራ ጠቅሰዋል፡፡
የከተማዋ ገቢዎ ቢሮ በበኩሉ በደረሰኝ ከሚደረግ ግብት ለመሸሽ ሸቀጦችን ወደ ሸገር ከተማ የሚያሸሹ ነጋዴዎች እንዳሉ መረጃው አለን፤በሁለቱም ከተሞች እንዲህ አይነቱን ህገ ወጥ ተግባር የሚፈፅሙ ነጋዴዎች ይዞ እርምጃ ለመውሰድ የአሰሳ ስራ እንጀምራለን ያሉን በቢሮው የታክስ ኢንቴሌጀንስና ምርመራ ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ተስፋዬ ነጋሽ ናቸው፡፡
በሰላምና ፀጥታ እንዲሁም ህገወጥ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠር በጋራ ያሰራናል ያሉትን ስምምነት የአዲስ አበባ ከተማ ሰላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ ሀላፊ ሊዲያ ግርማ እና የሸገር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪው አቶ ጉዮ ገልገሎ ፈርመውታል።
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 YouTube: https://t.ly/9uH-g
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il











Comments