ሰኔ 30 2017 - በወንጀል ድርጊት የተገኘ ገንዘብን ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብን ለመቆጣጠር በወጣው አዋጅ ላይ ''መርማሪው ከግድያ ውጭ የትኛውንም ድርጊት ቢፈጽም ተጠያቂ አይሆንም'' የሚለው ድንጋጌ እንዲወጣ ተደረገ
- sheger1021fm
- Jul 7
- 1 min read
በወንጀል ድርጊት የተገኘ ገንዘብን ወይም ንብረት ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብንና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በወጣው አዋጅ ላይ መርማሪው ከግድያ ውጭ የትኛውንም ድርጊት ቢፈጽም ተጠያቂ አይሆንም የሚለው ድንጋጌ እንዲወጣ ተደረገ፡፡
ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ በልዩ ስብሰባው፤ ከአሁን በፊት ውሳኔ የተሰጠበት ድንጋጌ እንዲታረም የቀረበለትን ረቂቅ አዋጅ አርሞ አፅድቋል፡፡
የሕግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ኢሳ ቦሩ ሪፖርት እና የውሳኔ ሃሳብ ያቀረቡ ሲሆን፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 37ኛ መደበኛ ስብሰባው፤ በወንጀል የተገኘ ንብረት ሕጋዊ ማስመሰል እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የቀረበ ረቂቅ አዋጅ፤ ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 1387/2017 አድርጎ ማፅደቁን አስታውሰዋል፡፡

ከአሁን በፊት የነበረው የረቂቅ አዋጅ ድንጋጌ እንዲታረም መደረጉ አተገባበሩ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ሊያስከትል ስለሚችል ረቂቅ አዋጁን ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን ሩ አቶ ኢሳ ቦሩ አስረድተዋል፡፡
የምክር ቤት አባላት አዋጁ ለሰብአዊ መብት ጥሰት በር የሚከፍት በመሆኑ ድንጋጌውን መሻሻሉ ተገቢ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ሰኔ 10/2017 ዓ.ም የጸደቀው በወንጀል የተገኘ ንብረት ሕጋዊ ማስመሰል እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳትን የሚመረምር ሰው፤ በምርመራ ወቅት ከአቅሙ በላይ በሆነ ምክንያት ከ #ግድያ ውጪ የትኛውንም ዓይነት ወንጀል ቢፈጽም ተጠያቂ የማያደርግ ነበር፡፡
አዋጁ በሽፋን ስር የሚደረግ ምርመራ (Under cover investigation) እንዲያስፈጽም የተመደበ ሰው፤ በግዴታ ላይ እያለ ከአቅሙ በላይ በሆነ ምክንያትና ከፈቃዱ ውጪ በሆኖ ከግድያ ወንጀል በስተቀር ለሚፈጽመው የወንጀል ድርጊት የወንጀል ክስ አይቀርብበትም ማለቱ ከፍተኛ ትችትና ተቃውሞ ቀርቦበት ነበር።
አሁን ይህ ከግድያ ወንጀል በስተቀር መርማሪው ለሚፈጽመው የወንጀል ድርጊት የወንጀል ክስ አይቀርብበትም የሚለው አንዲወጣ ተደርጎ አዋጁ ተሻሽሎ ጸድቋል፡፡
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il












Comments