ነሀሴ 16 2017 - የወባ በሽታ በስፋት የሚከሰትባቸው ወራት
- sheger1021fm
- Aug 22
- 2 min read
ከመስከረም እስከ ታህሳስ ያሉ ወራት የወባ በሽታ በስፋት የሚከሰትባቸው እንደሆኑ ይነገራል።
ህብረተሰቡም ከወዲሁ ጥንቃቄ እንዲያደርግ መልዕክቶች እየተላለፉ ነው።
በዚሁ ዙሪያ የሚሰራ አንድ ሀገር በቀል ድርጅት በበኩሉ የበሽታው ስርጭት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሆኖ የቀጠለበት አንዱ ምክንያት ስለ ህመሙ ያለ የተሳሳተ አረዳድ በመሆኑ እሱም ላይ መስራት ይገባል ብሏል።
በኢትዮጵያ አጠቃላይ የ #ወባ ስርጭት በስፋት የሚከሰተው ከመስከረም እስከ ታህሳስ ባሉ ወራት እንደሆነ የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የዘንድሮውን የክረምት ዝናብና በተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተውን ጎርፍ ተከትሎም ከመስከረም ወር አንስቶ በሽታው ሊከሰት ይችላል በሚል የጥንቃቄ መልዕክቶች እየተላለፉ ነው።
በየቦታው የተጠራቀመው የክረምቱ ዝናብ በቀጣይ ከሚኖረው ከፍተኛ ሙቀት ጋር ተዳምሮ ለበሽታው መስፋፋት ምቹ ሁኔታን ሊፈጠር ይችላል በሚል ነው መልዕክቱ እየተላለፈ የሚገኘው፡፡

ላለፉት 27 ዓመታት ይህንኑ በሽታ በመከላከል ዙሪያ ሲሰራ የቆየው የጤና ልማትና ፀረ ወባ ማህበርም ተመሳሳይ ጥሪ አቅርቧል።
ሰዎች ሊከላከሉት እና ታክመው ሊድኑ በሚችሉት ህመም መሞት የለባቸውም ሲሉ የማህበሩ ዋና ዳይሬክተር አቶ አበረ ምህረቴ ተናግረዋል።
የወባ በሽታ ስርጭት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሆኖ የቀጠለበት አንዱ ምክንያት ስለ ህመሙ ያለ አረዳድ እንደሆነ አቶ አበረ ተናግረዋል።
በተለይ ቀደም ባሉ ዓመታት በገጠሩ ክፍል ወባ በቆላማ አካባቢዎች የሚከሰት በሽታ ነው በሚል ሰዎች የጥንቃቄ ተግባራትን ከመፈጸም ቸል ይሉ እንደነበር አስታውሰዋል።
ወደ ጤና ተቋማት ለሄዱ ሰዎችም የሚሰጡ አንዳንድ የመድሃኒት አይነቶች ፈዋሽነት እንዳልነበራቸው ዳይሬክተሩ ጠቅሰዋል።
በእነዚህ መድሃኒቶች መዳን ያልቻሉ ሰዎች በተለይ በገጠሩ የኢትዮጵያ ክፍል በሽታውን ከሌላ ነገር ጋር እንዳያያዙት ፤ ይህም በተራው ጉዳቱን እንዳከፋው ጨምረው ተናግረዋል።
የዓለም ጤና ድርጅት እንደ ጎርጎርሳውያኑ አቆጣጠር በ2019 ይፋ ባደረገው መረጃ የወባ ሥርጭት በዓለም ላይ እየቀነሰ ይገኛል ማለቱ ይታወሳል።
የበሽታው ሥርጭት እየቀነሰባቸው ይገኛል ተብለው ከተጠቀሱ ሀገራት አንዷ ደግሞ ኢትዮጵያ ነበረች።
ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ ግን በኢትዮጵያ የበሽታው ስርጭት ዳግም እየሰፋ መምጣቱ ተነግሯል።
በኢትዮጵያ ከአጠቃላይ ህዝቡ 52 በመቶው ለወባ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች እንደሚኖር መረጃዎች ያሳያሉ።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ…. https://www.mixcloud.com/ShegerFM/45457/
ንጋቱ ረጋሳ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments