ሴቶች በዘርፉ የሚኖራቸው ተሳትፎ ሀገራዊ ዕንድምታም አለው ተብሏል።
በኢትዮጵያ በማምረቻው ዘርፍ ሴቶች ያላቸውን ተሳትፎ የተመለከተ የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው።
አለም አቀፉን የሴቶች ቀን 'ማርች 8"ን ምክንያት በማድረግ ውይይቱን ያዘጋጀው የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ነው።
የተለያዩ ተቋማትን የሚመሩ ሴት የስራ ሃላፊዎችም ልምዳቸውን በፓናል ውይይቱ ላይ አቅርበዋል።
በክብር እንግድነት የተገኙት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሃና አርአያስላሴ ሴቶች በማምረቻው ዘርፍ የሚያደርጉት ተሳትፎ ከተጠቃሚነታቸው ያለፈ እንድምታ አለው ብለዋል።
እንደ እሳቸው አባባል የህብረተሰቡ ግማሽ ቁጥር የሚይዙት ሴቶች በዘርፉ በቂ ተሳትፎ የላቸውም ማለት አገር በቂ ዕድገት እያስመዘገበች አይደለም ማለት ነው ሲል አስረድተዋል።
የተሳትፏቸው ዝቅተኛ መሆን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉድለት በአገር ላይ እንደሚያስከትል ሲናገሩ ሰምተናል።
የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ወይዘሮ መሠንበት ሸንቁጤ በበኩላቸው የገንዘብ ችግር ፣ መንግስታዊ ቢሮክራሲ እና ምቹ ያልሆኑ ፖሊሲዎች ሴቶች በማምረቻው ዘርፍ በበቂ ቁጥር ገብተው እንዳይሰሩ ካደረጉ ምክንያቶች መካከል እንደሆኑ ጠቅሰዋል።
ምክር ቤታቸው የንግድ ስራ ድጋፍ ለሴቶች በመስጠት በዘርፉ የሚኖራቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ የራሱን ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ አክለዋል።
ንጋቱ ረጋሳ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il