top of page

ጳጉሜ 3፣2015 - ከ300 ሺህ በላይ ዜጎች ለፓስፖርት አመልክተው በመጠባበቅ ላይ ናቸው ተባለ



በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ300 ሺህ በላይ ዜጎች ፓስፖርት ለማግኘት አመልክተው በመጠባበቅ ላይ ናቸው ተባለ፡፡


በፓስፖርት ምርት እጥረት ምክንያት አዲስ ፓስፖርት መስጠትም ሆነ እድሳት ለ6 ወር ያህል ተቋርጦ ቆይቷል፡፡


የእድሳትም ሆነ የአዲስ ፓስፖርት የመስጠት አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ዳግም ወደ ነበረበት መመለሱን የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ዛሬ በሰጠው መግለጫ ተናግሯል፡፡


የፓስፓርት ምርት እጥረት በማጋጠሙ ላለፉት 6 ወራት አገልግሎቱን አቋርጦ እንደነበረ የተናገሩት የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሠላማዊት ዳዊት ፓስፖርቱን የሚያመርቱት የውጭ ሀገር አምራቾች በኮቪድ 19 እና በሩሲያና ዩክሬይን መካከል ያለው ጦርነት የፓስፖርት እጥረት እንዲያጋጥም ምክንያት ሆነዋል ብለዋል።


ይህንን ችግር ለመፍታት አገልግሎቱ አምራች ድርጅቶችን በማነጋገር የፓስፖርት አገልግሎትን ለማስቀጠል ባሳለፍነው ወር 190 ሺህ ፓስፖርት አስገብተናል ብለዋል ዳይሬክተሯ።


በዚህም ባለፈው አንድ ወር 16712 ለሚሆኑ በመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ለሚኖሩ እና በአፍሪካ ሀገራት ደግሞ ለ4176 ሰዎች አገልግሎት እንዲያገኙ አድርገናል ብለዋል።


በተለያየ ምክንያት የፓስፖርት ቀጠሮአቸው ያለፈባቸው እና 90 ቀን ያልሞላቸው ከሆን በየሳምንቱ ቅዳሜ ቀን ወደ አገልግሎቱ መጥተው መስተናገድ ይችላሉ ተብሏል።


በአጠቃላይ በሀገር ውስጥ ከ300 ሺህ በላይ ሰዎች ፓስፖርት ፈላጊ አመልካቾች አሉ ተብሏል።



ፋሲካ ሙሉወርቅ


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ… https://bit.ly/33KMCqz




Comments


bottom of page