‘’ያጉት ፔይ ፋይናንሺል ቴክኖሎጂ’’ ከ’’ኢትስዊች’’ ጋር ባደረገው የፋይናንሺያል ቴክኖሎጂ ጥምረት አገልግሎት መስጠት ሊጀምር መሆኑን ተናገረ፡፡
ሁለቱ ኩባንያዎች ያደረጉት ጥምረት ለደንበኞች፣ ለነጋዴዎች እና ለባንኮች በርካታ ጥቅሞችን ይዞ የመጣ መሆኑ የተነገረለት ሲሆን በኢትዮጵያ ያለውን የዲጂታል ከፍያ ስርዓትን ለማሻሻል ይረዳል ተብሎ ታምኖበታል፡፡
ደንበኞች በኢትስዊች ኔትዎርክ አማካኝነት የየትኛውም ባንክ ካርድ በመጠቀም በ’’ያጉት ፔይ ፖስ’’ ግብይት እንዲያደርጉ ያስችላል ሲባል ሰምተናል፡፡
ነጋዴዎችም ከተለያዩ ባንኮች የሚቀርቡላቸውን የፖስ መሳሪያዎች ለመጠቀም በአማራጭነት የቀረበውን በአንድ የያጉት ፔይ ፖስ አገልግሎት መስጠት ይችሉሉ ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል ጥምረቱ ባንኮች በዋና የሥራ ዘርፋቸው ላይ እንዲያተኩሩ እና ወጪያቸውን በመቆጠብ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ ያስችላቸዋል ተብሎለታል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ አነስተኛ የንግድ ተቋማት የገንዘብ ፍሰታቸውን በተሻለ ሁኔታ እንዲያስተዳድሩ እና ቀልጣፋ የንግድ ልውውጦችን እንዲያደርጉ ይረዳል ተብሏል፡፡
ያጉት ፔይ ፋይናንሺያል ቴክኖሎጂ በመጪው በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የPOS ማሽኖች ቁጥርን ወደ 10000 ለማሳደግ እና ተደራሽነቱን ለማስፋት ማቀዱን ተነግሯል፡፡
ከዓመት በፊት የተመሰረተው ያጉት ፔይ ግለሰቦች የሞባይል ስልኮቻቸውን እና የመክፈያ ካርዶቻቸውን ተጠቅመው ክፍያዎችን እንዲያካሂዱ የሚያስችል ስማርት እና የሞባይል የክፍያ(POS) እንዲሁም ፔይመንት ጌትዌይ አገልግሎቶችን ያቀርባል፡፡
ንጋቱ ሙሉ
Comments