top of page

ጥቅምት 15፣2016 - ዳሸን ባንክ ከግብር በፊት 5 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ተናገረ

  • sheger1021fm
  • Oct 26, 2023
  • 2 min read

ዳሸን ባንክ በ2015 በጀት ዓመት ከግብር በፊት 5 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ተናገረ።


ይህም ከቀዳሚው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲመሳከር የ31.9 በመቶ ብልጫ አሳይቷል።


የዳሸን ባንክ የባለ አክሲዮኖች 30ኛ መደበኛ ጉባኤ በዛሬው እለት ተካሂዷል።


የባንኩ የቦርድ ሊቀመንበር አቶ ዱላ መኮንን ባንኩ በበጀት ዓመቱ 18 ቢሊዮን ብር ገቢ አስመዝግቧል ብለዋል።


ባንኩ ተጨማሪ 23.6 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰብ ችሏል ያሉት የቦርድ ሊቀመንበሩ ይህም ተቀማጩን 114.8 ቢሊዮን ብር አድርሶታል ብለዋል።


የባንኩ አጠቃላይ ሀብቱም 144.6 ቢሊዮን ብር ደርሷል ሲሉ ለባለ አክሲዮኖች ተናግረዋል።


የዳሸን ባንክ አጠቃላይ ካፒታሉ 19.3 ቢሊዮን ብር፤ የተከፈለ ካፒታሉ ደግሞ 9.3 ቢሊዮን ብር እንደደረሰ ተነግሯል።


የቦርድ ሊቀመንበሩ በባንኩ ዘርፍ ባለፈው በጀት ዓመት በርካታ አዳዲስ መመሪያዎች እንደወጡና የነበሩ መመሪያዎችም ማሻሻያ እንደተደረገባቸው አስታውሰዋል፡፡


እነዚህ መመሪያዎችም በባንኮች የሀብት መጠን፣ የስራ ማስኬጃና ተያያዥ ወጪዎችና ትርፋማነት ላይ የራሳቸው ተፅዕኖ እንደነበራቸው አስገንዝበዋል፡፡


አቶ ዱላ ባንኮች የግምጃ ቤት ሰነድ ግዥ እንዲፈፅሙ በድጋሚ የወጣው መመሪያ በብድር አቅርቦትና ገቢ ላይ ተጽዕኖ እንደነበረውም ጠቅሰዋል ፡፡


እያደገ የመጣው የዲጂታል መሰረተ ልማት ለረጅም ጊዜ በባንኮች ብቻ ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶች ከባንኮች ውጭ እንዲሰጡ እድል መፍጠሩንና ይህም ለባንኮች ጭምር ሰፊ እድል እንዲፈጠር ማድረጉን ተናግረዋል፡፡


የዳሽን ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ዓለሙ በበኩላቸው ያለፈው ዓመት ባንኩ ተደራሽነቱን ይበልጥ ከማስፍት አንጻር አዳዲስ ደንበኞችን ከማምጣትና ሀብት ከማሰባሰብ አኳያ እውንታዊ ውጤቶችን ያስመዘበበት ዓመት እንደነበር ጠቁመዋል፡፡


ዳሸን ባንክ ባለፈው በጀት ዓመቱ 253 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች መክፈቱንና አጠቃላይ የቅርንጫፎቹን ብዛት ከ835 በላይ መድረሳቸውን አስረድተዋል።


ከ5.2 ሚሊዮን በላይ ደንበኞች አሉኝ ያለው ዳሸን ባንክ የደንበኞቹን ፍላጎት የሚመጥኑ የባንክ አገልግሎቶችን መስጠቱን ይቀጥላል ብለዋል።


ዳሽን ባንክ በሀገሪቱ የግል ባንኮች ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን 40 ሚሊየን ዶላር የውጭ ብድር በቅርቡ ማግኘቱን ያስታወሱት አቶ አስፋው ይህም በዘርፉ ያለውን የውጭ ምንዛሬ ዕጥረት ከመቅረፍና የግብርና ምርት ወደ ውጭ ከመላክ አኳያ አውንታዊ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል ።


ዳሸን ባንክ ባለፈው በጀት ዓመት ማሀበራዊ ሃላፊነቱን ለመወጣት ከ285 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ አድርጌያለሁ ብሏል፡፡


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ… https://bit.ly/33KMCqz

Comentarios


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2025 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page