በአማራ ካልል ዳኞችን ከችሎት እያነሱ ማሰር እንዲቆም ብጠይቅም፤ ችግሩ ከቀድሞ ቢቀንስም እስራቱ ቀጥሏል ሲል የአማራ ክልል ዳኞች ማህበር ተናገረ፡፡
ማህበሩ ከህግ ወጭ ተይዘው ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ 4 ወር የሞላቸው ዳኞች መኖራቸውን ነግሮናል፡፡
ኢትዮጵያ ፈርማ ባጸደቀቻቸው አለም አቀፍ ህጎችም ሆነ በህገመንግስቱ ተጠርጣሪዎች ፍርድ ቤት መቅረብ የሚኖርባቸው በ48 ሰዓታት ውስጥ ነው፡፡
በክልሉ የታሰሩ ዳኞች ግን ፍርድ ቤት ሳይቅርቡ 3 እና 4 ወራት ሆኗቸዋል፡፡
ይህም ‘’አደገኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው ብለን እናምናል” ሲሉ የማህበር ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት አቶ ብርሃኑ አሳሳ ተናግረዋል፡፡
“በተለይም ከዳኝነት የስራ ባህሪ እና ከዳኝነት ነፃነት መርህ አንፃር ይህ ተግባር በእጅጉ ከህግ የሚጣረስ ነው” ይላሉ አቶ ብርሃኑ፡፡
ዳኞች ከችሎት ጭምር እየተወሰዱ ሲታሰሩ አብዛኞቹ የታሰሩበት ምክንያት እንኳን አልተነገራቸውም ተብሏል፡፡
“በእኛ በኩል ግን እንደታዘበ ነው ዳኞች እየታሰሩ ያሉት በነፃነት እንዲሰሩ በተሰየሙበት የዳኝነት ሙያ በሰጡት ፍርድ ምክንያት ነው” ብለዋል አቶ ብርሃኑ፡፡

በክልሉ 9ኝ ዳኞች በአሁኑ ወቅት በእስር ላይ መሆናቸውንም የአማራ ክልል ዳኞች ማህበር ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት አቶ ብርሃኑ ጠቁመዋል፡፡
በዳኞች ላይ ከህግ ወጭ የሚፈጸሙ እስራቶች የፍትህ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥሉ ናቸው ብለዋል፡፡
የዳኞች መታሰር የዳኝነት ነፃነትን ከመጋፋት ባሻገር እንደአጠቃላይ በፍትህ ሥርዓቱ ላይ አመኔታ ማጣቱን ያመጣል ብለዋል ማህበሩ፡፡
የዳኝነት ነፃነት መከበር ለሁሉም ነገር መሰረት ነው ያለው ማህበሩ ዜጎች በስርዓተ መንግስት እንዲተማመኑም ይረዳል ሲል አስረድቷል፡፡
በተለይ የአማራ ክልል ያለበት ሁኔታ ስለሚታወቅ በውጣ ወረድ ውስጥ አለፈው ፍትህ ፈልገው የሚመጡ ዜጎች የዳኞችን መታሰር ሲመለከቱ በተቋሙ ላይ እምነት እንያዲጡ ሊደርግ ስለሚችል እስራቱ እንዲቆም የታሰሩትም እንዲፈቱ ማህበሩ ጠይቋል፡፡
ዳኞች ከችሎች ተነስተው እንዲታሰሩ ሲደረግ አብዛኞቹ የታሰሩበት ምክንያት አልተገለፀላቸውም ሲል የአማራ ክልል ዳኞች ማህበር አስረድቷል፡፡
ዳኞቹ ተወስደው የታሰሩት አብዛኞቹ ከችሎት ከመኖሪያ ቤታቸው እና ከመንገድ ላይ እንደሆነም ሰምተናል፡፡
በጉዳዩ ላይ የክልሉን መንግስት ሃሳብ ለማካተት በተደጋጋሚ ያደርግነው ሙከራ አልተሳክም፡፡
ይሁንና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ከሳምንታት በፊት ለክልሉ ፕሬዝዳንት እና ለክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባዔ በፃፈው ደብዳቤ ችግሩ መኖሩን አረጋግጫለው ብሏል፡፡
ከድብዳቤው ላይ እንደተመለከትነው በፍርድ ቤት ስራ ላይ የአስፈፃሚው አካል ጣልቃ ገብነት መኖሩን ኢሰመኮ አረጋግጧል እንዲቆምም ጠይቋል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 YouTube: https://tinyurl.com/ky57kspd
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://tinyurl.com/yhycs5rs
Comments