top of page

ጥር  7፣2016  - የባህር ማዶ ወሬዎች

 

እስራኤል ውስጥ በተሰረቀ መኪና በርካታ ሰዎችን ሆን ብለው በመግጨት ጉዳት አድርሰዋል ተብለው የተጠረጠሩ ሁለት ግለሰቦች መያዛቸው ተሰማ፡፡

 

በተጠርጣሪነት የተያዙት ግለሰቦች ፍልስጤማውያን እንደሆኑ አረብ ኒውስ ፅፏል፡፡

 

18 ሰዎች ሲገጩ አንዲት ሴት በአደጋው እንደሞተች እና በተቀሩት ላይ አካላዊ ጉዳት እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡

 

ተጠርጣሪዎቹ ሆን ብለው ግጭቱን የፈፀሙት ራናና በተባለችዋ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች ነው ተብሏል፡፡

 

በግጭቱ ብርቱ ጉዳት የገጠማቸው ስላሉ የሟቾች ብዛት ሊጨምር እንደሚል ተገምቷል፡፡

 



 

የፍልስጤማውያኑ የጦር ድርጅት /ሐማስ/ ሁለት ታጋቾች በእስራኤል የአየር ድብደባ መገደላቸውን የሚያስረዳ አዲስ የቪዲዮ መልዕክት እዩልኝ ማለቱ ተሰማ፡፡

 

ሐማስ ሁለቱ ታጋቾች መሞታቸውን የሚያስረዳውን ቪዲዮ እዩልኝ ያለው ቀደም ሲል በሕይወት እንዳሉ የተቀረፀውን የቪዲዮ መልዕክት ካስተላለፈ ከ1 ቀን በኋላ እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡

 

የእስራኤል ጦር በሐማስ አዲስ የቪዲዮ መልዕክት ክፉኛ መቆጣቱ ታውቋል፡፡

 

ሐማስ የጦር ጫናው ስለበረታበት የፈጠረው ቅጥፈት ነው ማለቱ ተሰምቷል፡፡

 

የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ታጋቾቹ ነበሩበት የተባለው ሕንፃ በጭራሽ የአየር ድብደባ ዒላማችን አልነበረም ብለዋል፡፡

 

በቪዲዮ መልዕክቱ ላይ አንድ ሌላ ታጋች ሁለት አብረዋት የነበሩ ታጋቾች በእስራኤል የአየር ጥቃት ተገድለው በፍርስራሽ ስር መቀበራቸውን ስትናገር የሚደመጥበት እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡

 

የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር ዮአብ ጋላንት ዱላችን የበረታበት ሐማስ በእስራኤል ማህበረሰብ ላይ ስነ ልቦናዊ ጫና ለመፍጠር የዘየደው ቅጥፈት ነው ብለዋል፡፡

 

 

በአሜሪካ አዮዋ ሪፖብሊካዊውን የፖለቲካ ማህበር ወክሎ በፕሬዘዳንታዊ በእጩነት ለመቅረብ በተካሄደው ምርጫ የቀድሞው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሸነፉ፡፡

 

ትራምፕ ያሸነፉት ተፎካካሪዎቻቸውን በሰፊ ልዩነት በመብለጥ እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡

 

በፍሎሪዳ ደግሞ የግዛቲቱ አስተዳዳሪ ሮን ዲሳንቲስ በተባበሩት መንግስታት  የቀድሞዋን አምባሳደር ኒኪ ሐሌይን መርታታቸው ተሰምቷል፡፡

 

የሪፖብሊካዊውን የፖለቲካ ማህበር ወክሎ በፕሬዘዳንታዊ እጩነት የሚቀርብ ግለሰብ አሁን በስልጣን ላይ ከሚገኙት ዴሞክራቱ የአሜሪካ ፕሬዘዳት ጆ ባይደን ጋር እንደሚፎካከር ዘገባው አስታውሷል፡፡

 

 

ታንዛኒያ የኬኒያ አየር መንገድ የመንገደኞች ማጓጓዣ አውሮፕላኖች ድርሽ እንዳይሉባት ማገዷ ተሰማ፡፡

 

እገዳው ከሳምንት በኋላ ሙሉ በሙሉ ስራ ላይ እንደሚውል ዘ ኢስት አፍሪካን ፅፏል፡፡

 

ታንዛኒያ የኬኒያ ብሔራዊ አየር መንገድን ወደ ማገዱ እርምጃ የገባችው ኤር ታንዛኒያ የተሰኘው አየር መንገድ ከኬኒያዋ ርዕሰ ከተማ ናይሮቢ ወደ 3ኛ አገሮች የጭነት ማጓጓዝ ስራ እንዲያናውን በመከልከሉ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡

 

የኬኒያ አየር መንገድ በየሳምንቱ ወደ ታንዛኒያዋ የንግድ መናኸሪያ ዳሬሰላም 33 በረራዎችን ሲያደርግ መቆየቱን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 

እርምጃው ለወደፊቱ ታቅደው በነበሩ የመንገደኞች ጉዞዎች ላይ መስተጓጎል ሊያደርስ እንደሚችል ተገምቷል፡፡

 

በመጨረሻ የሁለቱ አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ችግሩን በ3 ቀናት ውስጥ በንግግር ለመፍታት መስማማታቸውን ቢቢሲ ፅፏል፡፡

 

 

የየመን ሁቲዎች ጂብራልተር ኢግል የተሰኘችን የጭነት መርከብ መምታታቸውን የአሜሪካ ሹሞች ተናገሩ፡፡

 

ጂብራልተር ኢግል የተመታችው ከኤደን ባህረ ሰላጤ በ160 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡

 

የተመታችዋ የጭነት መርከብ የአሜሪካ ነች ተብሏል፡፡

 

በጊዜውም የብረታ ብረት ምርቶችን ጭና እንደነበር በዘገባው ተጠቅሷል፡፡

 

ሁቲዎቹ ጂብራልተር ኢግልን የመቷት አሜሪካ እና ብሪታንያ ሰሞኑን በተከታታይ በየመን የሁቲዎቹን ይዞታ መደብደባቸውን በቀጠሉበት አጋጣሚ ነው፡፡

 

የተመታችዋ የጭነት መርከብ መለስተኛ ጉዳት አጋጥሟታል መባሉ ተሰምቷል፡፡

 

ርዕሰ ከተማዋ ሰንዓን ጨምሮ የየመን ሰሜናዊ ክፍል የሚያስተዳድሩት ሁቲዎች የኢራን ሁነኛ የጦር አጋሮች እና የፖለቲካ ወዳጆች መሆናቸው ይነገራል፡፡

 

እስራኤልየጋዛ የጦር ዘመቻዋን ካላቆመች ከእሷ ጋር አንዳች ቁርኝት ያላቸው እና መዳረሻቸውን የእስራኤል ወደቦችን ባደረጉ መርከቦች ላይ ጥቃት እያደረሱ ነው ይባላል፡፡

 

 

የኔነህ ከበደ

 

 

የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…

 

 

 

 

Comments


bottom of page