የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት የመገናኛ ብዙሃንና የጋዜጠኞች አጀንዳ ለይቶ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽነር አስረከበ።
ምክር ቤቱ ምክክር እንዲደረግባቸው የኢትዮጵያ ሚዲያን የሚመለከቱ 72 ጉዳዮች ለይቻለሁ ብሏል፡፡
ምክር ቤቱ በጉዳዮቹ ላይ በመወያየት 6 ዋና ዋና የሚዲያ ዘርፍ አጀንዳዎችን ለይቶ ለሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን በዛሬው እለት አስገብቷል፡፡
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት ምክክር እንዲደረግባቸው ከለያቸው ጉዳዮች መካከል የህዝብ ሚዲያ አስተዳደር፣ የመረጃ ነፃነት፣ መረጃ የማግኘት መብት ፣ ስርጭት እና ተደራሽነት የሚሉት ይገኙበታል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የፋይናንስ ዘላቂነት እና የማስታወቂያ ፍትሃዊነት ፣ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና ሚዲያ መሰረተ ልማት ፣ የጋዜጠኞች ጥበቃ ደህንነትና ዋስትና እና የሃላፊነት ውክልና ሚዛኑ ያልተስተካከለ የስርዓተ ፆታ ጉዳይ እና የጋዜጠኞች ሁኔታ የሚሉ አሉበት፡፡
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት ሰብሳቤ አቶ አማረ አረጋዊ ከላይ የተዘረዘሩት አጀንዳዎች የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃንና የጋዜጠኞች ጥያቄዎች ናቸው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ መገናኛ ብዙሃን ባለፉት 3 አመታት እንደ ሃገር እየተደረገ ያለው ሃገራዊ ምክክር ውጤታማ እንዲሆን አብሮን እየሰራ ነው ብለዋል።
ኮሞሽኑ በ1100 ወረዳዎች አጀንዳ የማሰባሰብ ስራ ተሰርቷል አብዛኛዎቹ ጥያቄዎች የሰላም ማስፈን፣ መልካም አስተዳደር እና ፍትህን የማስፈን ጥያቄዎች ናቸው ሲሉ ዋና ኮሚሽነሩ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን በአማራ ክልል አጀንዳ የማሰባሰቡን ስራ በሚቀጥሉት 3 ሳምንታት ለመጨረስ አቅዶ እየሰራ ይገኛል ተብሏል።
ከአማራ ክልል በመቀጠል በትግራይ ክልል የአጀንዳ ማሰባሰቡ ስራ ለመጀመር መታሰቡን ሲነገር ሰምተናል።
በረከት አካሉ
Comments