ጥር 17 2017 - በኢትዮጵያ በዓመት 10,000 እናቶች ህይወት ለመስጠት ብለው ህይወታቸውን ያጣሉ
- sheger1021fm
- Jan 25
- 1 min read
በኢትዮጵያ በዓመት 10,000 እናቶች ህይወት ለመስጠት ብለው ህይወታቸውን ያጣሉ።
የዛሬ 5 ዓመት የወጣ መረጃ እንደሚያሳየው በኢትዮጵያ ከሚወለዱ ከ1,000 ሕፃናት 5ተኛ ዓመት የልደት በዓላቸውን ሳያከብሩ የሚሞቱ ህፃት ቁጥር 53 ነው።
ይህንን የእናቶች እና ህፃናት ሞት ለመቀነስና የተሻለ ህክምና ለመስጠት በማሰብ የተከፈተው ‘’ማርህይወት የእናቶች እና ህጻናት ልዩ የህክምና ማዕከል’’ በዛሬው እለት ተመርቋል።
ማዕከሉን የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ሀላፊ ዮሐንስ ጫላ መርቀውታል።

እናቶች በጤና ተቋማት በባለሞያ ታግዘው እንዲወልዱ ለማድረግ በተደረገው ጥረት ህይወት ለመስጠት ብለው ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶችን ሞት እየቀነሰ መጥቷል፡፡
ነገር ግን አሁንም ከ100,000 እናቶች 267 እናቶች በወሊድና ተያያዥ ምክንያት ህይወታቸው ያልፋል፡፡
ይህን ሃላፊነት ታሳቢ በማድረግ ማርህይወት የእናቶች እና ህጻናት ልዩ የህክምና ማዕከል በዘርፉ ዘመናዊ ህክምናን ለመስጠት ራዕይ ይዞ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።

ይህ የህክምና ማዕከል ራሱ ባስገነባው ባለ 5 ወለል ህንጻ ላይ በ11 ስፔሻሊስት እና ሰብ ስፔሻሊስት ሃኪሞች አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል ተብሏል፡፡
ማዕከሉ እስካሁን ለህክምና ቁሳቁስ፣ ለግንባታና ለሌሎች አስፈላጊ ግብዓቶች ከ340 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ አድርጌያለሁ ብሏል፡፡
ማዕከሉ በጊዜያዊነት የሚሰሩትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች የስራ እድል ፈጥሯል፡፡
በመጪው አንድ ዓመት አቅም ለሌላቸው እናቶችና ህፃናት የሚውል ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ የህክምና አገልግሎትለመስጠት ማሰቡንም ተናግሯል።
በተጨማሪም በየ 3 ወሩ ሰራተኞችን አመራሮችንና ሌሎች በጎ ፍቃደኞችን በማስተባበር የደም ልገሳ የማድረግ ዕቅድ ይዧለሁ ብሏል፡፡
ንጋቱ ሙሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 YouTube: https://tinyurl.com/ky57kspd
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://tinyurl.com/yhycs5rs
Comments