በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በክረምት ወቅት ከዝናብ መክበድ ጋር በተገናኘ የጎርፍ አደጋ ደጋግሞ ተከስቷል።
በዚህም የሰው ህይወት ጠፍቷል፤ ነዋሪዎች ከአካባቢያቸው ተፈናቅለዋል፤ የንብረት ውድመትም አጋጥሟል።
ዘንድሮም መሰል ጉዳት ሊደርስ ይችላል በሚል ከወዲሁ ለጥንቃቄው ማሳሰቢያ እየተሰጠ ነው።
በአጠቃላይ ዘጠኝ ክልሎች ለጎርፍ ተጋላጭ ናቸው ተብለው እንደተለዩ የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን መረጃ አመልክቷል።

በእነዚህ ክልሎች ባሉ ወረዳዎች የሚገኙ እስከ አንድ ሚሊየን ሰዎች በጎርፍ አደጋ ሊፈናቀሉ ይችላሉ ነው የተባለው።
ጉዳቱን ለመቀነስ ከወዲሁ የቅድመ መከላከል ስራዎች እንዲከወኑ ከክልሎች ጋር ከሠሞኑ በበይነ መረብ ምክክር መካሄዱን፤ የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት እና የኮሙኒኬሽን ስራ አስፈጻሚ ተወካይ አቶ አታለለ አቦሃይ ነግረውናል።
በጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ስላለው ስጋት እንዲያውቁ ማድረግ አንዱ የቅድመ መከላከል ስራ ነው ተብሏል።
የከፋ የጎርፍ ተጋላጭነት በሚታይባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ለተወሰነ ጊዜ ለቀው እንዲሄዱ ማድረግም ሌላው የቅድመ መከላከል ስራ እንደሆነ ተነግሯል።
ከሳምንታት በፊት የአዲስ አበባ እና ድሬደዋ ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፤ በደረሱ የጎርፍ አደጋዎች የሰዎች ህይወት እንዳለፈ መነገሩ ይታወሳል።
ንጋቱ ረጋሳ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Youtube: http://tiny.cc/ShegerFM1021Radio
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments