ግንቦት 28 2017 - ሕብረት ኢንሹራንስ ''ሳካሄዳቸው የነበሩ ማህበራዊ ሀላፊነት የመወጣት ስራዎች ተሳክተውልኛል'' አለ
- sheger1021fm
- Jun 5
- 2 min read
ሕብረት ኢንሹራንስ የተመሰረትኩበትን 30ኛ ዓመት በማስመልከት፤ ሳካሄዳቸው የነበሩ ማህበራዊ ሀላፊነት የመወጣት ስራዎች ተሳክተውልኛል አለ።
ኩባንያው በ87 ባለአክሲዮኖች እ ኤ አ. በ1994 ፤ በ8 ሚሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል መመስረቱን አስታውሷል።
ሕብረት ኢንሹራንስ ከ30 ዓመታት በፊት በአንድ ቅርንጫፍ ቢሮ አገልግሎት መስጠት ጀምሮ በአሁኑ ወቅት በመላ ሀገሪቱ ከ71 በላይ የአገልግሎት መስጫ ማዕከሎች አሉኝ ብሏል።
ዛሬ ላይ የኩባንያው የተፈረመ ካፒታል 1.5 ቢሊዮን ብር ሲሆን ከዚህ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የተከፈለ ካፒታሉ ከ 1.3 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል ተብሏል፡፡
ጠቅላላ ሃብቱም 4.5 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስረድቷል።

ሕብረት ኢንሹራንስ ከ3ዐኛው ዓመት የምሥረታ በዓሉ ጋር በተያያዘ በርካታ የማኀበራዊ ኃላፊነት ስራዎች ሲያካሂድ መቆየቱን ነግሮናል።
ከእነዚህ ስራዎች መካከል 1.6 ሚሊዮን ብር ለግብረ ሰናይ ድርጅቶች የሰጠሁበት ይገኝበታል ብሏል።
በዚሁ መሠረት ለመቄዶንያ የአረጋዊያንና የአእምሮ ህሙማንን መርጃ ማዕከል 1 ሚሊየን ብር፣ ለህብረት ለበጎ በጎ አድራጎት ማህበር 400,000 ብር እና ለእውን በጎ አድራጎት ማህበር 200,000 ብር ድጋፍ ማድረጉን አስታውሷል።
ኩባንያው ከ30ኛ ዓመት ምስረታ በዓሉ ጋር ተያይዞ የሰራው ሌላው የማህበራዊ ሀላፊነት መወጣት ስራ ደም ልገሳ መሆኑን ጠቅሷል።
የደም ልገሳ መርሃ ግብሩ “ደም ይለግሱ፣ ሕይወትን ያጋሩ” በሚል መርህ ቃል ከኢትዮጵያ የደምና ሕብረህዋስ ባንክ ጋር በመተባበር በትናንትናው እለት ተከናውኗል።
በትናንቱ የበጎ ፈቃደኞች የደም ልገሳ መርሃ ግብር ላይ የኩባንያው ሰራተኞች እንዲሁም የከተማዋ ነዋሪዎች መሳተፋቸው የተነገረ ሲሆን ይህ የደም ልገሳ መርሃ ግብሩ የኩባንያው የ30ኛው ዓመት የምስረታ ክብረ በዓል የማጠቃለያ ፕሮግራም መሆኑም ተጠቅሷል፡፡

ሕብረት ኢንሹራንስ በ30 ዓመታት ጉዞው ዋነኛ ከተሰየመበት የኢንሹራንስ ስራ ጎን ለጎን በሃገሪቱ ባሉ ሜጋ ፕሮጀክቶች (ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ፣ ገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሃገር እና ገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች ማስፈፀሚያ) ድጋፍና የቦንድ ግዢ ማካሄዱን አስታውሷል።
በድሬዳዋ በደረሰው የጎርፍ አደጋ ምክንያት ህይወታቸው ችግር ውስጥ ገብቶ ለነበሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች እና በኮቪድ-19 ወረርሽን ወቅት በተከሰቱ ችግሮች ወቅት የፋይናንስ ድጋፍ ማድረጉንም አስረድቷል።
ለተለያዩ በጎ አድራጎት ድርጅቶች፣ ለኪነጥበቡ ዘርፍ፣ ለስፖርት፣ በመንግሥት እና ህዝብ ዘንድ በስፋት በአደባባይ እና በተለያዩ ሁኔታዎች ለሚከበሩ ሃገራዊ ክብረ በዓላት ማስፈፀሚያ የሚውል የገንዘብ ድጋፍ ሲያደርግ 30 ዓመታት እንዳለፈው ጠቅሷል።
ከተመሰረተ 30 ዓመት የሞላው ሕብረት ኢንሹራንስ "በ30 ዓመታት ታሪኬ ታላቅና አስደናቂ ዕድገት አስመዝግቤያለሁ" ማለቱ ይታወሳል፡፡
ንጋቱ ሙሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comentarios