በአዲስ አበባ ሲካሄድ የነበረው አጀንዳ የማሰባሰብ መድረክ ቢጠናቀቅም አጀንዳዎችን መቀበል እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተናገረ።
በአዲስ አበባ አጀንዳ አለን፤ ሊመከርበት ይገባል የሚሉት አጀንዳ ያላቸው ሁሉ ወደ ኮሚሽኑ በመምጣት ማቅረብ እንደሚችሉ የኢትዮጵያ ሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን ለሸገር አስረድቷል።
አሁንም ቢሆን በተናጠልም ይሁን በቡድን የሚቀርቡ አጀንዳዎችን ይዞ ወደ ኮሚሽኑ በአካል በመምጣትም ይሁን በኢሜል በመላክ ማስያዝ እንደሚቻል ኮሚሽነር አምባዬ ኡጋቶ ጠቁመዋል፡፡
በሂደቱ በጣም አስፈላጊና ሊመከርባቸው የሚገቡ አንገብጋቢ ጉዳዮች እንደተነሱ የሚናገሩት ኮሚሽነሩ ከዚህ በኋላ ለሚመጡ ጉዳዮችም በራችን ክፍት ነው ብለዋል፡፡
ለአንድ ሳምንት በነበረው አጀንዳ የማሰባሰብ ሂደት ከአዲስ አበባ የሚፈለገው አጀንዳ ተሰብስቧል ተብሏል፡፡
በዋናው ሃገራዊ ምክክር አዲስ አበባን ወክለው የሚሳተፉ ወኪሎችም ከተሳታፊዎቹ መካከል ይመረጣሉ፡፡
ስንጀምር በጣም አጣዳፊ፣ በጣም አስፈላጊና በጣም ወካይ በሚል አጀንዳዎቹን ለመለየት አስበን ብንመጣም የያዝነው አካሄድ ከህዝቡ ፍላጎት ጋር የሚሄድ ስላልነበር የያዝነውን ትተን ህዝቡ የሚፈልገውን አድርገናል የሚሉት ደግሞ ኮሚሽነር ዮናስ አዳዬ ናቸው፡፡
የነበረው አጀንዳ የማሰባሰብ ሂደት ህዝቡ በግልፅ የተወያየበት፣ባልተስማማባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ያለገደብ የተከራከረበት እንዲሁም የኢትዮጵያን ፖለቲካ ከጠብ መንጃ ወደ ምክክር ማምጣት እንደሚቻል ተስፋ የታየበት እንደሆነም ኮሚሽነሩ አንስተዋል፡፡
ምንታምር ፀጋው
Comments