የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤ/ክ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ አካባቢዎች 20 የትምህርት ቤት መገንቢያ ቦታዎችን ለመረከብ ተፈራርሜአለሁ አለች፡፡
የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርት ቤቶችን እንድትገነባባቸው የተሰጧት ቦታዎች 8ቱ በአዲስ አበባ እንዲሁም 12ቱ በኦሮሚያ ክልል ናቸው ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤ/ክ የጳጳሳት ጉባዬ ፕሬዚደንት ብጹዕ ካርዲናል ብርሀነ ኢየሱስ፤ ይህንን የተናገሩት ትናንት አዲሱ ገበያ አካባቢ የሚገኘው ''ላዛሪስት ካቶሊክ ት/ቤት የተመሰረተበትን 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል የመክፈቻ ዝግጅት ላይ ነው።
ካርዲናል ብርሀነ ኢየሱስ የካቶሊክ ቤተከርስቲያን በመላው ሀገሪቱ በትምህርት ልማት እያሰደረች ያለውን በጎ ተፅዕኖ ጠቅሰው፤ ለዚህ ስራዋ እውቅና እንደተሰጣትና እንድትበረታበትም በመንግስት መጠየቋን ተናግረዋል፡፡

የካቶሊክ በተክርስቲያን፤ በአዲስ አበባ ከአጸደ ህጻናት ጀምሮ እስከ መሰናዶ ያሉ 13 ትምህርት ቤቶች አሏት ተብሏል፡፡
በተለይም የሴቶች ትምህርት በሀገሪቱ እንዲበረታ ቤተክርስቲያኗ እንደምትጥር ካርዲናል ብርሀነ ኢየሱስ ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ የሚገኙት የልጃገረዶች ትምርት ቤት የሆኑትን ናዝሬት ስኩል፤ ፒያሳ አካባቢ የሚገኘው ካቴድራል የልጃገረዶች ት/ቤት እንዲሁም የቅድስት ድንግል ማርያም ትምህርት ቤትን ለዚህ በምሳሌነት አንስተዋቸዋል፡፡
በሌላ በኩል ከሰሜን ማዘጋጃ ወደ አዲሱ ገበያ መውጫ ያለው አውራ የአስፓልት መንገድ በስሙ እንዲሰየም ላዛሪስት ትምህርት ቤት ለከንቲባ ጽህፈት ቤት መጠየቁ ተሰምቷል።
ትምህርት ቤቱ ለከንቲባ ጽህፈት ቤት ላስገባው ደብዳቤም በጎ ምላሽ እየጠበቀ እንደሆነም ተናግሯል።
የትምህርት ቤቱ የበላይ ሀላፊ አባ ጌታሁን ፋንታ ይህንን የተናገሩት፤ ትምህርት ቤቱ የተመሰረተበትን 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል የመክፈቻ ዝግጅት ላይ ነው።
ትመህርት ቤቱ ከማስተማር ባሻገር፤ ለ100 ዓመት የአካባቢው ነዋሪዎችን ያገለገለ እና ብዙ አሻራ ያለው መሆኑ መንገዱ በስሙ እንዲሰየም ሊገባው የሚያደርግ ነው ብለዋል።
ንግድ ባንክ እና አቢሲኒያ ባንክ በአካባቢው የከፈቷቸው ቅርንጫፎቻቸውን በትምህርት ቤቱ ስም ማድረጋቸውም ለዚህ ማሳያ ነው ሲሉ አባ ጌታሁን ጠቅሰዋል።

ትመህርት ቤቱ ከ1917 ዓ.ም በመጀመር ተማሪዎችን እያስተማረ እንደቆየና በመጪው 2017 ዓ.ም አንድ ምዕት ዓመት ይደፍናል ተብሏል።
በአዲስ አበባ 2ኛ ቅርንጫፉን ለመከፈት አቅዷል የተባለው ይህ ትምህርት ቤት፤ የ100ኛ ዓመቱ ክብረ በዓል መሪ ቃል ደግሞ '' የአንድ ክፍለ ዘመን የላቀ ትምህርት የትውልድ ውርስ'' በሚል ተሰይሟል።
የካቶሊክ ቤተከርሰቲያን በመላው ሀገሪቱ ከ430 በላይ ትምህርት ቤቶችን ከፍታ ከአጸደ ህጻናት እስከ መሰናዶ ያሉ ተማሪዎችን እያስተማረች ትገኛለች ተብሏል፡፡
ማንያዘዋል ጌታሁን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Youtube: http://tiny.cc/ShegerFM1021Radio
Website: https://www.shegerfm.com/
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments