ግንቦት 1 2017 - በጡት ካንሰር ህመም መያዛቸው በህክምና ከሚረጋገጥ ሰዎች መካከል 60 በመቶዎቹ እንደሚሞቱ ተነገረ
- sheger1021fm
- May 9
- 2 min read
በኢትዮጵያ በየዓመቱ በጡት ካንሰር ህመም መያዛቸው በህክምና ከሚረጋገጥ ሰዎች መካከል 60 በመቶዎቹ እንደሚሞቱ ተነገረ፡፡
በሃገሪቱ በየዓመቱ ምን ያህል ሰዎች በጡት ካንሰር ህመም ይጠቃሉ የሚለውን ለማወቅ የተደረገ ጥናት ባይኖርም ከጤና ተቋማት የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው በየዓመቱ 17 ሺህ ያህል ሰዎች በጡት ካንሰር መያዛቸውን ያረጋግጣሉ፡፡
ከእነዚህ መካከል 9 ሺህ ያህሉ (60%) ለህልፈት እንደሚዳረጉ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ተናግሯል፡፡
ታማሚዎቹን ለዚህ የሚያበቃቸው ደግሞ አባዛኞቹ ተጠቂዎች ወደ ህመሙ እንዳለ በህክምና ለማረጋገጥ ባለሙያ ጋር የሚቀርቡት ህመሙ ጠንቶ መዳን ወደማይችልበት ደረጃ ከደረሰ በኋላ ስለሆነ ነውም ብሏል፡፡
ቢሮው ይህንን ያለው በጡት ካንሰር ህመም ግንዛቤ ማስጨበጥ ላይ እንደሚሰራ የሚናገረው ዘውዲቱ ጌታቸው መታሰቢያ ፋውንዴሽን ከአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ጋር በመሆን ለጤና ባለሙያዎች ባዘጋጀው የጡት ካንሰር ግንዛቤ ማስጨበጫ መርሃ ግብር ላይ ነው፡፡
ባለቤታቸው ከበድ ባለ የጡት ካንሰር ህመም በመጠቃታቸውና ህክምናቸውና ስለ ህመሙ ያለው የማህበረሰቡ የግንዛቤ ደረጃ ዝቅ ያለ መሆኑ አሳስቧቸው፤ ባለቤታቸውንም በህመሙ ምክንያት በሞት በማጣታቸው እርሳቸውን ለማሰብ በስማቸው ዘውዲቱ ጌታቸው መታሰቢያ ፋውንዴሽንን እንደመሰረቱ የነገሩን የፋውንዴሽኑ መስራችና ዋና ዳሬክተር እንዲሁም በሙያቸው በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ በጥቁር አንበሳ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ የፋርማሱቲካል ቴክኖሎጂ ፕሮፌሰር የሆኑት ፕሮፌሰር ፅጌ ገብረማሪያም ናቸው፡፡

ዋና ዳሬክተር ወደ ስራ ሲገቡ ማህበረሰቡ ስለ ጡት ካንሰር ያለው ግንዛቤ ከ50 በመቶ በታች መሆኑን ተመልክተው ይህንን ያስተካክላል ያሉትን የስልጠና ማንዋል አዘጋጅተው በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወደ ማሰልጠን እንደገቡ ነግረውናል፡፡
በከተማዋ ካሉ 11 ክፍለ ከተሞች ውስጥ ያሉ ጤና ጣቢያ ውስጥ ላሉ የጤና ባለሙያዎችን በማሰልጠን ማህበረሰቡ ጋር ለመድረስ ውጥን ይዘው ስራውን መጀመራቸውን የሚናገሩት ፕሮፌሰሩ ከጤና ቢሮ ጋር በመሆን በሚሰሩት የዘመቻ ስራ በተለይ ሴቶች 99 በመቶ ተጋላጭ እንደመሆናቸው ስለ ጡታቸው ያላቸው እውቀት የመልካቸውን ያልህ እስከሚሆን ድረስ እንደሚሰሩም ጠቁመዋል፡፡
በጡት ካንሰር በሽታ ተጠቅተው ለሞት የሚዳረጉ ነገር ግን ቁጥራቸው በውል የማታወቅ ሰዎች በርካታናቸው የተባለ ሲሆን በዚህ መንገድ የሚደረጉ ጥረቶች ትክክለኛውን ቁጥር ለማወቅ የሚሰራውን ስራ እንደሚያግዝም ተነግሯል፡፡
በኢትዮጵያ በገዳይነቱ ከደም ካንሰርና ከማህፀን በርጫፍ ካንሰር ቀጥሎ 3ኛ የሆነው የጡት ካንሰር ተጋላጭነቱና የጉዳቱ መጠን በትክክል አለመታወቁ አስጊ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
በአለም ዙሪያም በዓመት ከ600,000 በላይ ሰዎች በጡት ካንሰር ህመም እንደሚሞቱ ከባለሙያዎቹ ሰምተናል፡፡
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://shorturl.at/21bFN
留言