ያልተደራጀ የመረጃ አያያዝ እና ተቀናጅቶ አለመስራት የዓመቱ የባህል፣ስፖርት እና ኪነ ጥበብ ዘርፍ ክፍተት መሆኑን ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ተናገረ ።
- Aug 5
- 1 min read
ሐምሌ 29 2018
ያልተደራጀ የመረጃ አያያዝ እና ተቀናጅቶ አለመስራት የዓመቱ የባህል፣ስፖርት እና ኪነ ጥበብ ዘርፍ ክፍተት መሆኑን ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ተናገረ ።
ከስፖርት ዘርፍ ስኬት አንፃር የሚቀርቡ ትችቶችን ለማስተካከል በሀገር ደረጃ በዚህ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ የፀደቀው የስፖርት ልማት እና አስተዳደር አዋጅ ተስፋ ተደርጎበታል።
ይህ የተባለው የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የ2018 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ እያደረገ ባለበት መድረክ ላይ ነው።
በጉባኤው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ባህልና ስፖርት ሚንስትር ወ/ሮ ሸዊት ሻንካ ዘንድሮ ክፍተት የታየባቸውን የመረጃ አያያዝ እና ተቀናጅቶ የመስራት ችግሮችን በቀጣዩ ዓመት ትኩረት ሰጥተን አሰንሰራበታለን ብለዋል።
በኪነ ጥበብ ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታት የጥበብ ምክር ቤት ፖሊሲ እየተዘጋጀ መሆኑንም ሚንስትሯ አንስተዋል።
ከ28 ዓመት በኋላ ተሻሽሎ የፀደቀው የስፖርት ልማት ፖሊሲ የግል ባለሃብቶችን ወደ ዘርፉ ለማምጣት ይረዳል ብለዋል።
በዓመቱ ብዙም ትኩረት ያልተሰጠው የሰርከስ ስፖርት የተሻለ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ሚንስትሯ ጠቅሰዋል ።
በዚህም በዘርፉ ኢትዮጵያ 12 የዓለም ክብረ ወሰኖችን የያዘች ሲሆን 4 መቶ 15 ሚሊየን ብር ገቢ ተገኝቶበታል ብለዋል።
በዓመቱ 52 ብሔራዊ በዓላት መከበራቸውን ያነሱት ወ/ሮ ሸዊት ከእነዚህም 47ቱ የዘመን መለወጫ በዓላት ናቸውም ጠቅሰዋል።
የኢትዮጵያን የስፓርት ዘርፍ ለማሳደግ በታዳጊዎች ላይ መስራት አለብን ያሉት ወ/ሮ ሸዊት በሀገር አቀፍ ከ1ሺህ 5 መቶ በላይ የማሰልጠኛ ጣቢያዎች 49 ሺህ በላይ ታዳጊዎችን በስፖርት እያበቃን ነው ብለዋል።
ዛሬ በጀመረው የባህልና ስፖርት ሚንስቴር የ2018 የማጠቃለያ ጉባኤ መድረክ የአፈፃፀም ሪፖርቶች ፣የመጪው አመት ዕቅዶች እና ጥናቶች ላይ የባለድርሻ አካላት ውይይት ያደርጉባቸዋል ተብሏል።
በጉባኤው የሚንስቴር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች፣የክልል ቢሮ ኃላፊዎች፣ምሁራኖች እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች የተገኙ ሲሆን እስከ ነሃሴ 1/2018 ዓ.ም ይቀጥላል።
ንጋት መኮንን
_edited.jpg)




Comments