የጥቅምት 7፣2017 - የሞቱ ምክንያት ገና ሳይታወቅ፤ የህክምና ስህተት ነው በሚል ሞያተኞች እንደሚታሰሩ፣ እንደሚንገላቱ ይህም ፈተና መሆኑን የጤና ሚኒስቴር ተናግሯል
- sheger1021fm
- Oct 17, 2024
- 1 min read
አንድ ሰው ህክምና እያደረገ ህይወቱ ቢያልፍ ለሞት ያበቃው ምክንያት ገና ሳይታወቅ፤ የህክምና ስህተት ነው በሚል ሞያተኞች እንደሚታሰሩ፣ እንደሚንገላቱ ይህም ፈተና መሆኑን የጤና ሚኒስቴር ተናግሯል፡፡
ይህንንም ለማስተካከል ያገዛል የተባለ የጤና አዋጅ ፓርላማ መድረሱንም ሰምተናል፡፡
ከዚህ ባለፈም የጤና ባለሞያዎች በተለይ በአንስቴዥያ ህክምና የጤና ባለሞያዎቹ ራሳቸውን የሚጠብቁበት በቂ የሆነ የህክምና የደህንነት ቁሶች ባለመሟላቱ ለጤና መታወክ ብሎም ለሞት እየተጋለጡ መሆኑን የኢትዮጵያ አንስቴቲስቶች ማህበር ተናግሯል።
የኢትዮጵያ አንስቴቲስቶች ማህበር ም/ፕሬዚዳንት አቶ እያየአለም መለሰ በጤናው ዘርፍ በተለይ በአንስቴዥያ ህክምና ላይ በርካታ ችግሮች እንዳሉ አንስተው የህክምና ባለሙያዎቹ ለታካሚዎች በሚሰጡት የህክምና አገልግሎት በሚገጥም የህይወት ህልፈት ምንነቱ እና ምክንያቱ ገና ባለተጣራበት ሁኔታ የጸጥታ ኃይሎች የሚያደርጉት አፈሳ እና እንግልት ተገቢ አይደለም ብለዋል።
የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አየለ ተሾመ(ዶ/ር) በበኩላቸው በጤና ባለሙያዎች ላይ እየደረሰ ያለው እስር እና እንግልት ለማስቆም የጤና ሚኒስቴር ከተለያዩ ተቋማት ጋር በፌዴራልና በክልል ደረጃ እየሰራበት መሆኑን አንስተው ይሄ ጉዳይ እልባት እንዲያገኝ እና በህግ አግባብ እንዲዳኝ ለማድረግ በህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ በጤና አዋጁ ላይ እየተወያየበት በመሆኑ መፍትሄ የሚገኝበት ይሆናል ብለዋል።
ፍቅሩ አምባቸው












Comments