ትናንት ማምሻውን በፈንታሌና መተሃራ አካባቢ የተከሰተው የመሬት መንቀጥቅ ከእስካሁኖቹ ሁሉ በመጣም ከፍተኛው ነው ተባለ፡፡
ይህም እንቅስቃሴው እንደሚቀጥል የሚያሳይ በመሆኑ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግም ተጠይቋል፡፡
ትናንት ምሽት 5 ሰዓት ከ28 ደቂቃ ላይ የተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ በሬክተር ስኬል 6 ሆኖ መዝገቡን በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጂኦፊዚክስ ፣ ህዋ ሳይንስና አስትሮኖሚ ተቋም የቴክኖሎጂ ባለሙያ እና የት/ት ክፍሉ ሃላፊ የሆኑት ፕሮፌሰር አታላይ አየለ ለሸገር ተናግረዋል፡፡

የመሬት መንቀጥቀጡ ከመሬት ወለል በታች እስከ 20 ኪሎ ሜትር ጥልቀት ላይ የተከሰተ በመሆኑ ጉዳት አላስከተለም፤ አዲስ አበባ ላይም ንዝረቱ እምብዛም ያልተሰማው ለዚህ ነው ብለውናል፡፡
ባለፉት ወራት የተከሰቱት የመሬት መንቀጥቀጦች ከመሬት ወለል በታች 10 ኪሎ ሜትር ላይ ይከሰቱ እንደነበር ጠቅሰው የአሁኑ ከዛ በበለጠ በጥልቀት የተከሰተ ሆኖ እንጂ በሬክተር ስኬል 6 የተመዘገበ ርዕደ መሬት ውድመት የሚያስከትል ነው ብለዋል፡፡
በርግጥ አሁንም ከፈንታሌ በ6 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ባለው መተሃራ ከተማ ምን እንደተፈጠረ እስካሁን አላረጋገጥንም፤ ጉዳት እንዳልደረሰ ተስፋ እንዳደርጋለን ብለዋል፡፡
ትዕግስት ዘሪሁን
コメント