ከኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር ኮንዶምን የሚጠቀሙት ወንዶች 20 በመቶ ብቻ መሆናቸውንና የሴቶቹ ቁጥር 50 በመቶ እንደሚደርስ ጥናት አሳየ፡፡
ባለፈው 2016 ዓ.ም በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ የተከወነው የማህበረሰብ ጤና ጥናት ይህንን አሳይቷል፤ለዚህ ደግሞ የኮንዶም እጥረት እና የማህበረሰቡ ግንዛቤ ማነስ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ፡፡
ይህ የተባለው በየዓመቱ የካቲት 6 የሚከበረው የዓለም የኮንዶም ቀን በፖሊስ ሆስፒታል በተከበረበት ወቅት ነው፡፡
የኤች አይቪ ኤድስ ቫይረስንና የአባላዘር በሽታዎችን ለመከላከል ጥቅም ላይ የሚውለውን ኮንዶም የሚጠቀመው ሰው ቁጥር ከግማሽ ያልዘለለ ቢሆንም ፍላጎቱ 270ሚሊዮን አቅርቦቱ ግን ከ90 ሚሊዮን ያልዘለለ ነው ተብሏል፡፡
አቶ ቶሎሳ ኦላና በዚህ ጉዳይ ላይ ከሚሰሩ ተቋማት መካከል በሆነው ኤድስ ሄልዝ ኬር ፋውንዴሽን የመከላከልና አፍሪካ ዩኒየን ላያዘንና አድቮኬሲ ማናጀር ናቸው፡፡

በየዓመቱ ከ3 ሚሊዮን በላይ ኮንዶም ወደ ሃገር ቤት እያስገባሁ በነፃ ለማህበረሰቡ እያከፋፈልኩ ነው የሚለው ድርጅቱ የአቅርቦት እጥረቱን መቅረፍ እንዳልተቻለ አቶ ቶሎሳ ነግረወርናል፡፡
በተለይም መለዮ ለባሽ የሆኑት ፖሊስ፣መከላከያና የማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ባልደረቦች ለኤች አይቪ ቫይረስ ይበልጥ ተጋላጭ ከሆኑት መካከል መሆናቸውን የሚናገሩት ሃላፊው የፀጥታ አካላቱን የኮንዶም አጠቃቀም ባህል ለማሳደግ በዛሬው እለት 200 ሺህ ኮንዶሞችን ኤኤች ኤፍ የተባለው ግብረ ሰናይ ድርጅት አበርክቷል ብለዋል፡፡
የጤና ሚኒስቴር በበኩሉ አደረግኩት ባለው ቅኝት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በ800 የመንግስት የጤና ተቋማት ተመርምረው በደማቸው የኤች አይ ቪ ቫይረስ ከተገኘባቸው ግለሰቦች መካከል 13 በመቶዎቹ መለዮ ለባሾቹ የፀጥታአካላት ሆነው አግኝቻቸዋለሁ ብሏል፡፡
ስለጉዳዩ የጠየቅናቸው የፌድራል ፖሊስና የማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን የስራ ሃላፊዎች በሰጡን ምላሽ በየመስሪያ ቤቶቻቸው የቫይረሱን ስርጭት መለቆጣጠር ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ ይሰራል፤በስራ ቦታ ኮንዶም ለፖሊስ አባላቱ እንደሚቀመጥላቸው ነግረውናል፡፡
በማረሚያ ቤቶችም ታራሚዎች ከእስር ሲፈቱ ኮንዶም እንደሚታደል አስረድተዋል፡፡
ይሁንና የኮንዶም እጥረት በመኖሩ የመከላከል ስራውን ፈታኝ አድርጎብናል ብለውናል፡፡
ምንታምር ፀጋው
Comentários