top of page

የካቲት 7፣2016 - ዋሻ ውስጥ እያሉ አፈር የተናደባቸው የኦፓል ማዕድን አውጭዎች እስካሁን አልተገኙም ተባለ

በደቡብ ወሎ ዞን በዋሻ ውስጥ እያሉ አፈር የተናደባቸው የኦፓል ማዕድን አውጭዎች እስካሁን አልተገኙም ተባለ፡፡


በደቡብ ወሎ ዞን ደላንታ ወረዳ በተለምዶ ‘’ቆቅ ውሃ’’ እየተባለ በሚጠራ አካባቢ ወጣቶች የኦፓል ማዕድን እያወጡ በነበረበት ወቅት ነው ዋሻው እንደተናደባቸው የተነገረው፡፡


ወጣቶቹን ለማውጣትም የቦታው አቀማመጥ ለማሽን የተመቸ ባለመሆኑ በሰው ኃይል በቁፋሮ ህይወታቸውን ለማትረፍ ጥረት እየተደረገ ቢሆንም ካለ ምንም መፍትሄ ስድስት ቀናትን እንዳስቆጠሩ የደላንታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አያሌው በሪሁን ለሸገር ተናግረዋል።


ይህ መሳዩ ችግር በዞኑ ሲከሰት የመጀመሪያ እንዳልሆነ የተናገሩት አቶ አያሌው ቁጥራቸው በውል ባይታወቅም ከስምንት እስከ አስር የሚሆኑ ሰዎች የአደጋው ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉ ተገምቷል ብለዋል፡፡


የነፍስ አድን ስራው ችግሩ ከተፈጠረበት ቀን ጀምሮ እየተሰራ ቢሆንም ተስፋ የሚሰጥ ነገር ግን እየታየ አለመሆኑን ሸገር ከወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ሰምቷል፡፡


ዋና አስተዳዳሪ የኦፓል ማዕድን አውጭዎቹ በምን ያህል እርቀት ውስጥ ተቀብረው እንዳሉ በውል አይታቅም፣ የነፍስ አድን ስራውን የሚከውኑ ሰዎች ግን እስከ 70 ሜትር ድረስ መቆፈራቸውን ተናግረዋል፡፡ ያም ሆኖ ግን ተስፋ የሚሰጥ ነገር እንዳልታየ ነው የሰማነው፡፡


ወጣቶቹን ለማውጣት ወረዳው የቻለውን እየሰራ መሆኑን የተናገሩት አቶ አያሌው የበለጠ ድጋፍ ተደርጎልን ሰዎቹን ለማውጣት ከክልሉም ሆነ ከፌደራል አካላት እየተነጋገርን ነው ብለዋል፡፡


ወጣቶች በማህበር ተደራጅተው በባህላዊ መንገድ የኦፓል ማዕድን በወረዳው ማውጣት የጀመሩት ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ ነው ተብሏል፡፡


ፋሲካ ሙሉወርቅ



የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…



Comments


bottom of page