የግብር ዕዳ እያለባቸው ለመክፈል ፍቃደኛ ያልሆኑ 62 ግለሰቦች ያፈሩትን ሃብት ላለባቸው እዳ ማካካሻ እንደሚያውለው የገቢዎች ቢሮ ተናግሯል፡፡
የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ ከፋይናንስ ኢንቴሌጀንስ አስተዳደር ጋር በመሆን የግብር እዳቸውን ያልከፈሉኝን ግለሰቦችና ተቋማት እያደንኩ ነው ሲል በተደጋጋሚ ሲናገር ቆይቷል፡፡
ካለፈው ዓመት ጀምሮ ሳይከፈል ከተከማቸው ከ11 ቢሊዮን ብር በላይ የሆነ እዳ ከ6.4ቢሊዮን ብር በላዩን በዚህ ዓመት በመንፈቅ ጊዜ ውስጥ አስከፍያለሁ የሚለው ቢሮው፤ ቀሪውን 4.6 ቢሊዮን ብር #የግብር_እዳ ያልከፈሉኝን የማደኑ ስራ እንደቀጠለ ነው ብሏል፡፡
ካልተከፈለው ውስጥ 3.2 ቢሊዮን ብሩን ያልከፈሉት 62 ግለሰቦች ናቸው፤ በተደጋጋሚ እዳቸውን እንዲከፍሉ ጥሪ ቢደረግላቸውም ሊከፍሉ ባለመቻላቸው ከሃገር እንዳይወጡ ታግደዋል፡፡
ከዚህ በኋላም ንብረታቸው ታግዶ ላልከፈሉት እዳ ማካካሻ ይውላል ያሉን የቢሮው የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ ናቸው፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ከአጠቃላዩ የግብር እዳ የሚቀረው 1.3 ቢሊዮን ብር እዳ ያለባቸው ሌሎች ግለሰቦችም አሉ የሚሉት አቶ ሰውነት እነዚህም ነጋዴዎች እዳቸውን የሚከፍሉት በተመሳሳይ መንገድ እንደሆነና ማንነታቸውን የማጣራት ስራው እንደሚቀጥል ጠቅሰዋል፡፡
ሌሎችም ግብር የሚሰውሩ፤ያለ ደረሰኝ ሲሰሩ የተገኙ ነጋዴዎች እየተቀጡ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በዚህም በተያዘው ዓመት ከ111 ቢሊዮን ብር በላይ ከገቢ ግብር መሰብሰቡን አቶ ሰውነት ነግረውናል፡፡
ግብር ከፋዮች ከፍ ያለ ግብር ሲጣልባቸው ጉዳዩን ወደ ግብር አቤቱታ ከመውሰድ ይልቅ ግብር ሳይከፍሉ የመጥፋት ዝንባሌ እንዳላቸው ይጠቀሳል፡፡
ቢሮው ከዚህ ይልቅ ጉዳያችሁን ወደ ግብር አቤቱታ ብትወስዱት መፍትሄ ልሰጣችሁ ዝግጁ ነኝ ብሏል፡፡
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Website: https://shorturl.at/yCz7q
📌 YouTube: https://tinyurl.com/ky57kspd
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://tinyurl.com/yhycs5r
Comentários