የዛምቢያው ፕሬዘዳንት ሐኪይንዴ ሒቺሌማ አገሪቱን በገጠማት ከባድ ድርቅ ምክንያት የአስቸኳይ ጊዜ ማወጃቸው ተሰማ፡፡
ፕሬዘዳንቱ አገሪቱ ካሏት 116 ወረዳዎች በ84ቱ ከባድ ድርቅ ማጋጠሙን እንደተናገሩ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
ቀደም ሲል በአገሪቱ ዝናብ ቢጠበቅም መጠኑ እጅግ አነስተኛ ሆኖ መቅረቱ በዘገባው ተጠቅሷል፡፡
ዛምቢያ ከዚምባብዌ ጋር ለሐይድሮ ኤሌክትሪክ ማመንጫነት የምታውለው የካሪባ ግድብም የያዘው የውሃ መጠን መያዝ ከሚገባው ከ12 በመቶ በታች ነው ተብሏል፡፡
ከግድቡ ሀይል ማመንጨት ከማይቻልበት ደረጃ መድረሱ ተጠቅሷል፡፡
ከሁሉም በላይ የተዘራው ሰብል እንዳለ ክው ማለቱን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የሶማሊያ የቀድሞ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፋውዚያ ዩሱፍ አዳም ለአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበርነት ሊፎካከሩ ነው፡፡
የሶማሊያ መንግስት ለፋውዚያ ዩሱፍ አዳም ድጋፍ ማሰባሰብ መያዙን ዘ ኢስት አፍሪካን ፅፏል፡፡
በኬኒያም የዋነኛው ተቃዋሚ ጥምረት መሪ ራይላ ኦዲንጋም ለህብረቱ ኮሚሽን ሊቀመንበርነት የምረጡኝ ዘመቻ መጀመራቸው ተጠቅሷል፡፡
ኦዲንጋን የኬኒያው ፕሬዘዳንት ዊሊያም ሩቶም በምርጫ ዘመቻው እየረዷቸው ነው ተብሏል፡፡
ፋውዚያ ዩሱፍ አዳም በቀዳሚው የፕሬዘዳንት ሐሰን ሼክ ማሀሙድ አስተዳደር ዘመን በውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ማገልገላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሆኖ የሚመረጥ ግለሰብ አሁን በሀላፊነት ላይ የሚገኙት ቻዳዊውን ዲፕሎማት ሙሳ ፋቂ ማህማትን ይተካቸዋል፡፡
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ምርጫ ከአመት በኋላ ይከናወናል፡፡
በባንግላዴሽ ርዕሰ ከተማ ዳካ በባለ 6 ፎቅ የገበያ ማዕከል ሕንፃ ላይ የደረሰ ቃጠሎ በጥቂቱ 43 ሰዎችን መግደሉ ተሰማ፡፡
በአደጋው ጉዳት የደረሰባቸው ሌሎች 22 ሰዎች ደግሞ ወደ ሆስፒታል እንደተወሰዱ አሶሼትድ ፕሬስ ፅፏል፡፡
ጉዳት ከደረሰባቸው መካከል ለሕይወታቸውም የሚያሰጋቸው አሉ ተብሏል፡፡
ከአደጋው ለማምለጥ ከሕንፃ ወደ ምድር ሲዘሉ ሕይወታቸው ያለፈም እንዳሉ ተጠቅሷል፡፡
የአደጋ ተከላካይ ሰራተኞች ከ70 ያላነሱ ሰዎች በሕይወት ማውጣታቸው ታውቋል፡፡
ቃጠሎው በምን ምክንያት እንደተቀሰቀሰ ለጊዜው አልተነገረም፡፡
በባንግላዴሽ የመኖሪያ እና የንግድ ማከናወኛ ህንፃዎች የእሳት አደጋ እንደሚደጋገም ቢቢሲ አስታውሷል፡፡
በጋዛ የእስራኤል ጦር በፈፀመው ድብደባ እርዳታ ለመቀበል ተሰልፈው ሲጠባበቁ ከነበሩ ፍልስጤማውያን መካከል ከ100 በላይ የሚሆኑት መገደላቸው ተሰማ፡፡
በእርዳታ ጠባቂዎቹ ላይ የተፈፀመው ግድያ ከየአቅጣጫው እየተኮነነ መሆኑን TRT ዎርልድ ፅፏል፡፡
የዋይት ሐውስ ሹሞች ሪፖርቱ ደርሶናል ብርቱ አደጋ ነው ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
ለማውገዝ ግን አልደፈሩም ተብሏል፡፡
እስራኤል በሐማስ ላይ ያነጣጠረው የጋዛ ዘመቻዬ ራስን ለመከላከል የታለመ ነው ባይ ነች፡፡
የአሜሪካም መንግስት ይሄንኑ አቋም እንደሚጋራ በተግባር ጭምር አስመስክሯል ተብሏል፡፡
ንብረትነቱ የኤር ታንዛኒያ አየር መንገድ የሆነ የመንገደኞች አውሮፕላን ለበረራ እንደተነሳ በገጠመው የሞተር እክል ከከባድ አደጋ መትረፉ ተሰማ፡፡
አውሮፕላኑ በሰላም ቢነሳም አየር ላይ ከባድ የሞተር እክል ስለገጠመው ወዲያው በዳሬሰላም በሚገኘው ጁሊየስ ኔሬሬ አለም አቀፍ ኤርፖርት እንዳረፈ ዘ ኢስት አፍሪካን ፅፏል፡፡
የሞተር እክሉ በመንገደኞቹ ክፍል ሳይቀር ከባድ ጭስ አስነስቶ ነበር ተብሏል፡፡
ራስን መሳት የገጠማቸው መንገደኞች እንደነበሩ በዘባው ተጠቅሷል፡፡
አውሮፕላኑ 112 መንገደኞች እና ሰራተኞችን አሳፍሮ ነበር ተብሏል፡፡
አብዛኞቹ ተሳፋሪዎች አውሮፕላን ተቀይሮላቸው መብረራቸው ታውቋል፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Telegram: https://tinyurl.com/yc6tfzsw
Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments